Sunday, September 24, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ቦርድ ዋና ጸሐፊውን አገደ

ተዛማጅ ፅሁፎች

የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ቦርድ፣ የንግድ ምክር ቤቱን ዋና ጸሐፊ ከሥራ እንዲታገዱ ወሰነ፡፡

ዘጠኝ አባላት ያሉትና በአቶ ሰለሞን አፈወርቅ የሚመራው የንግድ ምክር ቤቱ ቦርድ፣ ዋና ጸሐፊው አቶ ጋሻው ደበበ ከኃላፊነታቸው እንዲታገዱ ውሳኔ ያሳለፈው ባለፈው ሐሙስ ጥቅምት 25 ቀን 2008 ዓ.ም. እንደሆነ ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ቦርዱ በዋና ጸሐፊው ላይ የዕገዳ ዕርምጃውን የወሰደበት ዋነኛ ምክንያት ግልጽ ባይሆንም፣ ከሥራ የታገዱ መሆናቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ በንግድ ምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት በኩል ተፈርሞ እንዲደርሳቸው ቦርዱ ከስምምነት ላይ መድረሱ ታውቋል፡፡

ለጉዳዩ ቅርበት ካላቸው ወገኖች እንደተሰማው፣ በቦርዱና በዋና ጸሐፊው መካከል ከዚህም ቀደም በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ አለመግባባቶች ነበሩ፡፡ በዚህም ምክንያት እንዲህ ያለው ዕርምጃ ይጠበቅ ነበር ይላሉ ምንጮች፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞም ቦርዱ በንግድ ምክር ቤቱ ወቅታዊ እንቅስቃሴዎች ላይ አሉ የሚባሉ ችግሮችን ሲያሰባስብ እንደነበር ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በተለይ ንግድ ምክር ቤቱ በቅርቡ ባካሄደው ጠቅላላ ጉባዔና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ዕውቅና በሰጠበት ፕሮግራም ላይ ታየ የተባለው የፕሮግራም መፋለስና ጉድለት፣ የቦርድ አባላቱን አስቆጥቶ ነበር ተብሏል፡፡ በዚህ ምክንያትም አለመግባባት ተፈጥሮ እንደነበር በማስታወስ፣ የዋና ጸሐፊው ከሥራ መታገድ አንደኛው ምክንያት ከዚህ ጋር የተያያዘ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት የሚሰነዝሩ አሉ፡፡

የቦርዱ ዕገዳ ጊዜያዊ ይሁን ሙሉ በሙሉ ከሥራ ማሰናበትን የሚያጠቃልል መሆኑ ማረጋገጫ አልተገኘም፡፡ በሌላ በኩል ግን አቶ ጋሻው ከዚህ ውሳኔ በፊት መልቀቂያ ሳያስገቡ እንዳልቀሩ ይነገራል፡፡

ቦርዱ በአቶ ጋሻው ላይ እንዲወሰድ የወሰነው ዕርምጃ ንግድ ምክር ቤቱ በየዓመቱ በሚያካሂደውና ባለፈው ሐሙስ በይፋ በተከፈተው ‹‹የኢትዮጵያን ይግዙ›› ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት መክፈቻ ዕለት መሆኑ ደግሞ፣ ጉዳዩን አነጋጋሪ አድርጎታል፡፡

በዕለቱ አቶ ጋሻው የንግድ ትርዒቱን የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት ሲመሩ እንደነበር፣  የመክፈቻ ፕሮግራሙ ከተጠናቀቀ በኋላ ቦርዱ ተሰብስቦ ውሳኔውን ማሳለፉ የምንጮች መረጃ ያመለክታል፡፡

አቶ ጋሻው ንግድ ምክር ቤቱን ከስድስት ዓመታት በላይ በዋና ጸሐፊነት በመምራት፣ በንግድ ምክር ቤቱ ረዘም ላለ ጊዜ በያዙት ኃላፊነት የቆዩ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

በእሳቸው ዋና ጸሐፊነት ወቅት አራት ፕሬዚዳንቶች የተፈራረቁ መሆኑም፣ አቶ ጋሻው ከሌሎች ዋና ጸሐፊዎች በተለየ በቦታው የቆዩ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው ተብሏል፡፡

ወደ ንግድ ምክር ቤቱ ከመምጣታቸው ቀደም ብሎ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና በንግድ ሚኒስቴር አገልግለዋል፡፡    

በንግድ ምክር ቤቱ ቦርድ ዕገዳ የተደረገባቸውን አቶ ጋሻውንና የቦርድ ሰብሳቢውን አቶ ሰለሞን ሪፖርተር ለማነጋገር ጥረት ቢያደርግም፣ ሁለቱንም በአካልም ሆነ በስልክ ለማግኘት አልተቻለም፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች