ሦስተኛውን ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባዔ በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ጥቅምት 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ያከናወነው የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማኅበር፣ ለአንጋፋው የስፖርት ጋዜጠኛ ሰለሞን ገብረ እግዚአብሔር ዕውቅናና የገንዘብ ሽልማት አበረከተ፡፡
የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማኅበር እንደ ሙያ ማኅበር ከተመሠረተ ዓመታትን ቢያስቆጥርም፣ ይህ ነው የሚባል እንቅስቃሴ ሳያደርግ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ከሦስት ዓመት በፊት እንደ አዲስ ተቋቁሞ እንቅስቃሴውን የጀመረው ይኼው ማኅበር፣ አሁንም በሁለት እግሩ ቆሞ መሄድ በሚያስችለው ሁኔታ ላይ አለመገኘቱ ጥቅምት 26 ቀን 2008 ዓ.ም. በዳሸን ቢራ ስፖንሰር አድራጊነት በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ለሦስተኛ ጊዜ በተከናወነው ጉባዔ ተመልክቷል፡፡
ይሁንና ማኅበሩ ኢትዮጵያ መሥራች በሆነችበት የአፍሪካ እግር ኳስ ዋንጫ ለሦስተኛ ጊዜ በ1968 ዓ.ም. ካዘጋጀችው አሥረኛው የአፍሪካ ዋንጫ በኋላ ወደ መድረኩ ለመግባት የወሰደባትን ስድስት ዓመታት ሰብሮ፣ ምዕራብ አፍሪካዊቷ ጊኒን አሸንፎ ለስኬት የበቃው የአሠልጣኝ መንግሥቱ ወርቁ ቡድን ገድል በዕማኝነት ለታሪክ ካስቀሩት ጋዜጠኞች አንዱ ሰለሞን ገብረ እግዚአብሔር ነበር፡፡ በወቅቱ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የስፖርት ጋዜጠኛ ሰለሞን የጋዜጠኝነት ሕይወቱን ከጀመረ ሦስተኛ ዓመቱ ላይ ይገኝ ነበር፡፡ ዘንድሮ 37ኛ ዓመቱ ላይ ሲደርስ ለአራት አሥርታት ግድም በአንጋፋነት ለቆየበትና ለወጣት ስፖርት ጋዜጠኝነት አርዓያነቱ፣ የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማኅበር ዕውቅናና የ10,000 ብር የገንዘብ ሽልማት አበርክቶለታል፡፡
ሰለሞን ብዙዎች ከሚያተኩሩበት እግር ኳስና አትሌቲክስ ባሻገር እምብዛም ቦታ ለማይሰጣቸው ስፖርቶች ትኩረት በመስጠት ረገድ ግንባር ቀደም ስለመሆኑም በርካቶች ይስማሙበታል፡፡ ሽልማቱ ከተሰጠው በኋላም ወጣቶቹ የስፖርት ጋዜጠኞች ለሌሎች ስፖርቶች ትኩረት እንዲሰጡ ጠይቋል፡፡ (ለዚህ ዘገባ ሔኖክ ያሬድ አስተዋጽኦ አድርጓል)