የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን፣ 15,761,674 ብር የሚገመቱ የመድኃኒት፣ የምግብና የመዋቢያ ዕቃዎች ጥራታቸውን ባለመጠበቃቸውና የባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱን ደንብና መመርያ ተከትለው ባለመምጣታቸው ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ ማገዱን አስታወቀ፡፡
ባለሥልጣኑ ለሪፖርተር በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ በ2008 ዓ.ም. የመጀመሪያው ሩብ ዓመት፣ በማዕከላዊ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት በተደረገው ቁጥጥር በቦሌ ዓለም አቀፍ ተርሚናል፣ በቦሌ ካርጎ፣ በኮሜት፣ በሞጆና አዳማ መግቢያ መውጫ ኬላዎች በተደረገ ጥብቅ የጤና ቁጥጥር ወደ አገር ውስጥ ሊገቡ የነበሩ 11,517,890 ብር የሚጠጋ ጥራታቸው፣ ደህንነታቸውና ፈዋሽነታቸውን ያልጠበቁ መድኃኒቶች፣ 4,079,168 ብር በላይ የሚሆኑ ጥራታቸው ያልተረጋገጡ ምግቦችና 168,616 ብር የሚገመት የመዋቢያና የፅዳት ዕቃዎችን ይዟል፡፡
በተጨማሪም የባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱን ደንብና መመርያ የማያሟሉ የምግብ ማምረቻ፣ አስመጪና አከፋፋይ ላይ እርምጃ የወሰደ ሲሆን የያዟቸው ምርቶች እንዲወገዱ ተደርጓል፡፡ በድርጅቶቹም ላይ ከብቃት ማረጋገጫ ስረዛ እስከ ጽሑፍ ማስጠንቀቂያ መሰጠቱን ገልጿል፡፡
በሩብ ዓመቱ 4,003,883,207 ብር በላይ የሚያወጡ መድኃኒቶች፣ የሕክምና መሣሪያዎችና የውበትና የንጽህና መጠበቂያ ግብአቶች ላይ ቁጥጥር ተደርጎባቸው ወደ አገር ውስጥ የገቡ ሲሆን፣ የባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ የጤና ግብአቶችና አገልግሎቶች ጥራታቸውን ለማስጠበቅ ቁጥጥሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥል በማስታወቅ፣ ኅብረተሰቡ ሕገወጦችን በማጋለጡ ሒደት የበኩሉን እንዲጫወት ጥሪ አቅርቧል፡፡