በደቡብ ክልል በሰገን አካባቢ ሕዝቦች ዞን ሥር ካሉ ስምንት ብሔረሰቦች መካከል አንዱ የሆነው የኮንሶ ሕዝቦች ዞን የመሆን ጥያቄ ከክልሉ ድጋፍ እንዳላገኘ ተገለጸ፡፡
የሰገን አካባቢ ሕዝቦች ዞን በ2003 ዓ.ም. ከተዋቀረ ጀምሮ የኮንሶ ሕዝቦች በተለያየ መልኩ ይህንኑ ጥያቄ ለማቅረብ እንደሞከሩ የተጠቆመ ሲሆን፣ መስከረም 29 ቀን 2008 ዓ.ም. 50,033 ሰዎች በተገኙበት ስብሰባ ይህንኑ ጉዳይ የሚያስፈጽሙ 12 ተወካዮች መመረጣቸውም ታውቋል፡፡ ይህም በሕግ የሚጠየቀውን የአምስት በመቶ ፊርማ ለማሟላት ከእጥፍ በላይ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
ከኮሚቴው አባላት መካከል አቶ (ካላ) ገዛኸኝ ወልደ ዳዊት ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ክልሉ አሁን በሥራ ላይ ያለው መዋቅር እንዲለወጥ ፍላጎት የለውም፡፡ የኮንሶ ሕዝቦች በአንፃሩ ከሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ ከመልካም አስተዳደር ዕጦት፣ ከማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትና ከማንነት አኳያ አሁን ካለበት የወረዳ አደረጃጀት ወደ ዞንነት ለመሸጋገር በቂ ምክንያቶች እንዳሉት ገልጸዋል፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱና የአገሪቱ ሕግ በሚፈቅደው መሠረት በሕዝብ ብዛት፣ በተማረ የሰው ኃይል ብዛትና በመልክዓ ምድር መሥፈርቶችን እንደሚያሟላም ጠቁመዋል፡፡
በሰገን አካባቢ ሕዝቦች ዞን ስምንት ብሔረሰቦች የሚገኙ ሲሆን እነዚህም ኮንሶ፣ አሌ፣ ቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ኩሱሜ፣ ሞሴና ማሽሌ ናቸው፡፡ በተጨማሪም ዞኑ በአምስት ወረዳዎች የተዋቀረ ሲሆን፣ እነዚህም አሌ ልዩ ወረዳና ደራሼ፣ ኮንሶ፣ አማሮና ቡርጂ ወረዳዎች ናቸው፡፡
እንደ አቶ ገዛኸኝ ገለጻ፣ የብሔረሰቡ ተወካዮች በክልልና በፌዴራል መንግሥት ለሚመለከታቸው አካላት ጥያቄ እያቀረቡ ነው፡፡ በተለይ ለደቡብ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት ጥያቄውን ከማቅረባቸው በፊት ለሰገን አካባቢ ሕዝቦች ዞን ጥያቄውን በቅድሚያ አቅርበዋል፡፡ ከዞኑ አስተዳዳሪ ለየት ያለ ተቃውሞ እንደደረሰባቸው ያመለከቱት አቶ ገዛኸኝ፣ ከክልሉ ኃላፊዎች ጋር በተለያየ ጊዜ ውይይት በማድረግ ጉዳዩ ሕጋዊና ሰላማዊ መፍትሔ እንዲያገኝ መጣራቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ይሁንና ከቅርብ ሳምንታት ጀምሮ የክልሉ ኃላፊዎች ለውይይት ወደ ኮንሶ ወረዳ ከመጡ በኋላ ውጥረት እንደነገሠ ገልጸዋል፡፡ ከተመረጡት መካከል ሦስት ሰዎች መታሰራቸውንም ገልጸዋል፡፡
‹‹ይባስ ብሎ ጉዳዩ የሕዝቡ ሳይሆን የጥቂት ግለሰቦች ነው በሚል ተለጣፊ ስም እየተሰጠን ነው፡፡ የግንቦት 7 እና የሰማያዊ ፓርቲዎች አስፈጻሚዎች ተደርገን ነው ስማችን እየጠፋ ያለው፡፡ የክልሉ ልዩ ኃይል ወደ ወረዳችን ከመጣ በኋላ ያለው ድባብ አስፈሪ ነው፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ደግሞ ጉዳያችሁ በክልል ተወስኖ በይግባኝ ካልመጣችሁ በቀጥታ ጉዳዩን አናስተናግድም ብሎናል፤›› ብለዋል፡፡
የኮሚቴው አባላት ጥያቄአቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት፣ ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ ለሰብዓዊ መብት ኮሚሽንና ለፌዴራልና አርብቶ አደሮች ልማት ጉዳዮች ጨምሮ ለተለያዩ የመንግሥት ተቋማት አቅርበዋል፡፡
ሪፖርተር ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ያገኘው መረጃ እንደሚጠቁመው የመዋቅር ለውጥ ጉዳይ ላይ ምክር ቤቱ የዳኝነት ሥልጣን የለውም፡፡ የማንነት ጥሰት ካልሆነ ይህ አስተዳደራዊ ጉዳይ በክልሉ ማለቅ ይኖርበታል፡፡ ሪፖርተር ከደቡብ ክልል በጉዳዩ ላይ መረጃ ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡