ከምርጫ 97 በኋላ ዓለም አቀፍ ለጋሾች የቀጥታ የበጀት ድጋፋቸውን በመቀየር፣ ላለፉት አሥር ዓመታት ተግባራዊ ሲያደርጉት የቆየው የመሠረታዊ አገልግሎቶች ከለላ ድጋፍ ላይ ማሻሻያ ሊያደርጉ መሆኑ ታወቀ፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥትና ለጋሾች የጋራ የበጀትና የዕርዳታ ግምገማ ኅዳር 6 ቀን 2008 ዓ.ም. በግዮን ሆቴል በተጀመረበት ወቅት ነው ማሻሻያው እንደሚደረግ የተገለጸው፡፡
‹‹ማንኛውም የልማት እንቅስቃሴ ወደ ሌላ ደረጃ እንደሚሸጋገረው ሁሉ፣ የመሠረታዊ አገልግሎቶች ድጋፍ ወደ ሌላ ደረጃ መሸጋገር እንዳለበት የኢትዮጵያ የልማት አጋሮች አምነናል፤›› በማለት የለጋሾች ቡድን የጋራ መግለጫ ያስረዳል፡፡
ማሻሻያው ያስፈለገበት ምክንያት ደግሞ የበጀት አጠቃቀም ላይ የበለጠ ግልጽነትን ለመፍጠር፣ የሰው ሀብት ልማት ላይ ትኩረት ለማድረግና የየክልሉን ተጨባጭ ሁኔታ ከግንዛቤ ያስገባ እንዲሆን ለማድረግ ነው ብለዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትር ዴኤታው አቶ አህመድ ሽዴ ቀጣዩ ፕሮግራም “Enhancing shared prosperity through Equitable services – ESPES” (የጋራ ብልፅግናን በፍትሐዊ አገልግሎቶች ማሳደግ) እንደሚባል ገልጸዋል፡፡
አሁን ባለው ሥርዓት ለጋሾች በዓመት የሚያደርጉት ድጋፍ በፌዴራል መንግሥት አማካይነት ለክልሎች በድጐማ የሚተላለፍና ክልሎች እንደየተጨባጭ ሁኔታዎቻቸው መሠረታዊ አገልግሎቶችን የሚሰጡበት ነው፡፡ ይህንን የድጋፍ አሰጣጥ በመቀየር ተግባራዊ የሚደረገው አዲሱ አሠራር እ.ኤ.አ. ከ2016 ጀምሮ ለሦስት ዓመታት ተግባራዊ የሚደረግ ነው፡፡
‹‹የመሠረታዊ አገልግሎቶች ከለላ ፕሮግራም እየወጣ ነው የሚሄደው፡፡ አዲስ የሚጀመረው ፕሮግራም ዓላማውና አተገባበሩም ተመሳሳይ ነው፡፡ ሆኖም ግን የሚሠሩ ሥራዎች ቅንጅትና የትኩረት አቅጣጫ ለውጥ ይደረግበታል፡፡ ዋናው ዓላማም አገልግሎቱ ለሁሉም ተደራሽ የሚሆንበትና የሁሉንም ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ መልኩ ይቃኛል፤›› ሲሉ አቶ አህመድ ገልጸዋል፡፡
የመሠረታዊ አገልግሎቶች ከለላ ከምርጫ 97 በኋላ ለጋሾች ለመንግሥት ቀጥታ የሚያደርጉትን ድጋፍ በማቋረጥ፣ የአገሪቱ ማኅበረሰቦች መሠረታዊ ድጋፍ እንዳያጡ የቀረፁት ፕሮግራም ቢሆንም፣ መንግሥት በዚህ የድጋፍ ፕሮግራም የተሻለ መጠቀሙን ይገልጻል፡፡
በመሠረታዊ አገልግሎቶች ከለላ ድጋፍ ሥር ተግባራዊ የሚደረጉ ፕሮጀክቶች የውኃ፣ የትምህርት፣ ጤና፣ የገጠር መንገድና የመሳሰሉት ማኅበራዊ ፕሮጀክቶች ናቸው፡፡ በለጋሾች በኩል የፕሮጀክቱ አፈጻጸም ውጤታማ ቢሆንም፣ ታዳጊ ክልሎች ድጋፉን ከመጠበቅ ባለፈ ሀብት መፍጠር እንዳልቻሉ ይገልጻሉ፡፡