የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከዘጠኝ ዓመታት በፊት ሥራ በጀመረ ጊዜ የአባልነት ወንበር የያዙ አባላት ድርሻቸውን የገዙት በ50 ሺሕ ብር እንደነበር ይታወሳል፡፡ ሁለት ዓይነት የአባልነት ሒደትን በመከተል ሲንቀሳቀስ የቆየው ምርት ገበያው፣ በመጀመርያው ዙር አባልነትን በዝቅተኛ ዋጋ ካስገኘው የወንበር ሽያጭ በኋላ በተለያዩ ጊዜያት በአባላት ጥያቄ፣ ምርት ገበያውም በራሱ ተጨማሪ ወንበሮችን በማካተት የአባልነት ወንበር የሚያስገኘውን ዕድል በጨረታ ማቅረብ ጀምሮ በዚያው አግባብ ሲሠራ ቆይቷል፡፡
በዚሁ መሠረት የአባልነት አሠራር መሠረት ለወንበር ግዥ የሚቀርበው የጨረታ ዋጋ በሚሊዮን ብሮች እየተቆረጠለትና ፉክክሩ የዜና ሽፋን እያገኘ መምጣቱ ይታወሳል፡፡ ይሁንና በሳምንቱ አጋማሽ ወቅት ምርት ገበያው አምስት የአባልነት ወንበሮችን ለመሸጥ ባወጣው ጨረታ ተጫራቾች አሸናፊ የሆኑበት ዋጋም ይኼንኑ ነባር አካሔድ አመላክቷል፡፡ በሽያጭና ግዢው ሒደት የሚሳተፉ አባላት የወንበሮቻቸው ዋጋ ከሌላው ጊዜ ጨምሮ መምጣቱ ታይቷል፡፡
ለአምስት የአባልነት ወንበሮች የተካሔደው ጨረታን በማስመልከት የወጣው የምርት ገበያው መረጃ የሚያሳየው፣ በጨረታ ያሸነፉ ግለሰብ ነጋዴዎችና ኩባንያዎች የሰጡት ዋጋ እስከ 3.5 ሚሊዮን ብር እንደደረሰ ነው፡፡
በጨረታው 15 ግለሰቦችና ኩባንያዎች የተሳተፉ ሲሆን፣ ከእነዚህ ተጫራቾች ውስጥ ከፍተኛውን ዋጋ የሰጡ ኩባንያዎችና ግለሰቦች የጨረታው አሸናፊ ሆነው የተመረጡበትን ከፍተኛ ዋጋ ያቀረቡት አምስት ተጫራቾች ናቸው፡፡ ከአምስቱ ኩባንያዎች በዝቅተኛ ዋጋ አሸናፊ የሆነው በ1.5 ሚሊዮን ብር የቀረበው የጨረታ ሒደት ሲሆን፣ ከፍተኛው 3.5 ሚሊዮን ብር እንደሆነም ማወቅ ተችሏል፡፡
እንዲህ ዓይነቱ ጨረታ የአባልነት ድርሻቸው እንዲሸጥላቸው ለሚጠይቁ አባላት በየሩብ ዓመቱ የሚወጣበት አሠራር ሲሆን፣ በሳምንቱ አጋማሽ የተካሄደው ጨረታም ምርት ገበያው ሥራውን በጀመረበት ወቅት አንድ የአባልነት መቀመጫ በ50,000 ብር ይሸጥ እንደነበር ያስታወሰበት አጋጣሚ ነበር፡፡ ለአባልነት የቀረበው ከፍተኛው ገንዘብ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ787 ሺሕ ብር ብልጫ እንደታየበት ምርት ገበያው አስታውቋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በምርት ገበያው የሚያገበያዩ 347 አባላት አሉ፡፡ የአባልነት ወንበር ማንኛውም ሕጋዊ ሰው ወይም ድርጅት በምርት ገበያ የመገበያየት መብት አለው፡፡ የመገበያየት መብት የሚያስገኘው ወንበር ሁለት ዓይነት የአባልነት መደቦችም አሉት፡፡ ተገበያይና አገናኝ አባል በመባል ይታወቃሉ፡፡ ተገበያይ አባል የሚገበያየው በራሱ ስም ብቻ ሲሆን፣ አገናኝ አባል ግን በራሱ ወይም በደንበኞች ስም መገበያየት የሚችልበት የአባልነት ዓይነት ነው፡፡ ደንበኛ በመባል የሚታወቁት ተገበያዮች ግን ማንኛውም ሕጋዊ ሰው ወይም ድርጅት መሆናቸው ተጠብቆ፣ በአገናኝ አባላት በኩል የሚገበያዩት ናቸው፡፡
መደበኛ ተገበያይ አባላትና አገናኝ አባላት የአባልነት ወንበሮችን በምርት ገበያው ተቀባይነት ላለው ሰው ወይም ድርጅት ማስተላለፍ ይችላሉ፡፡ የአባልነት ወንበር የሚያስተላልፍ አባል አስፈላጊውን ዕውቅና ካገኘ በኋላ፣ ቢያንስ ለሦስት ዓመታት በምርት ገበያው አባልነት የመቆየትና በምርት ገበያው ደንብ የተቀመጡ ሌሎች መሥፈርቶችን ማሟላት እንደሚጠበቅበት የምርት ገበያው አሠራር ይጠቅሳል፡፡
የአባልነት ወንበርን በሽያጭ ማስተላለፍን በተመለከተ ከምርት ገበያው የተገኘው መረጃ እንደሚያስረዳው፣ ሰሞኑን እንደተካሄደው ዓይነት የአባልነት ወንበር ሽያጭ የሚካሄደው በአባላት ጥያቄ ነው፡፡ የአባልነት ወንበር ይሸጥልን የሚሉ አባላት ለሽያጭ ያበቃቸው ምክንያት ታይቶና ተፈትሾ ተቀባይነት ካገኘ ተራ እንዲይዙ ተደርጎ፣ ሽያጩ ይከናወንላቸዋል፡፡ ከሽያጩ የሚገኘው ገንዘብ በቀጥታ ይደርሳቸዋል፡፡ ይህ አሠራር በዓመት አራት ጊዜ ይከናወናል፡፡
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የአባልነት ወንበራቸውን ለመሸጥ ጥያቄ ከሚያቀርቡት ውስጥ አብዛኞቹ በሚገጥማቸው ኪሳራ ሳቢያ ነው፡፡ የአባልነት ወንበር ለመሸጥ ያመለከቱ አባላት በቅርቡ በሚካሄደው አምስተኛው ዙር የጨረታ ሒደት ድርሻቸውን እንደሚሸጡ ይጠበቃል፡፡