– ቤቱ ለባለቤቱ እንዲመለስ ከተወሰነ 17 ዓመታት አልፎታል
የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 17 ቀበሌ 19 ውስጥ የሚገኘውን፣ የቤት ቁጥር 119 የሆነውንና የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናትና ምርምር ማዕከል ዋና ዳይሬክተር አቶ በረከት ስምዖን እየኖሩበት የሚገኘውን መኖሪያ ቤት፣ ታኅሳስ 18 ቀን 2008 ዓ.ም. እንዲያስረክብ ታዘዘ፡፡
ኤጀንሲው ቤቱን ለባለ ንብረቱ አቶ መሐሪ ተወልደ ብርሃን እንዲያስረክብ፣ የኢትዮጵያ ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ከ17 ዓመታት በፊት ሚያዝያ 28 ቀን 1990 ዓ.ም. ትዕዛዝ ያስተላለፈ ቢሆንም፣ በተለያዩ ምክንያቶች እስካሁን አለማስረከቡ ተጠቁሟል፡፡
የቤቱ ባለቤት አቶ መሐሪ ጥቅምት 5 ቀን 1988 ዓ.ም. ለፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ባቀረቡት አቤቱታ እንዳስታወቁት፣ ቤቱ የተወረሰው ከአዋጅ ውጪ በመሆኑ እንዲመለስላቸው መጠየቃቸውን ሰነዶች ያስረዳሉ፡፡ ኤጀንሲውም ባደረገው ምርመራ የአመልካቹ ቤት በአዋጅ ቁጥር 110/87 አንቀጽ 2(3) መሠረት ከአዋጅ ውጪ የተወረሰ መሆኑን እንዳረጋገጠ ጠቁሞ፣ ኤጀንሲው ለቤቱ ማሠሪያ የዋለ የባንክ ዕዳ ካለ ተሳስቦ ለባንክ እንዲከፍልና ምንም ዓይነት የዕዳ ጥያቄ ሳያቀርብ ቤቱን ለአቶ መሐሪ እንዲያስረክብ አዞት እንደነበር ሰነዱ ያሳያል፡፡ ነገር ግን ቤቱ ተጨማሪ ማጣራት እንደሚያስፈልገው ተገልጾ፣ ከሰኔ 12 ቀን 1990 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ታኅሳስ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ድረስ ታግዶ የቆየ ቢሆንም፣ ቤቱ እንዲመለስላቸው የተሰጠው ውሳኔ ትክክል መሆኑ ስለተረጋገጠ፣ የፕራይቬታይዜሽንና የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ኤጀንሲ ቦርድ እግዱ እንዲነሳ ጥር 1 ቀን 2006 ዓ.ም. በመወሰኑ፣ ቤቶች ኤጀንሲ ቤቱን ለአቶ መሐሪ እንዲያስረክብ በድጋሚ ማዘዙን ሰነዶች ያስረዳሉ፡፡
ቤቶች ኤጀንሲ እንዲያስፈጽም ለተላለፈለት ትዕዛዝ በሰጠው ምላሽ፣ ‹‹ቤቱ ለባለቤቱ እንዲመለስ ውሳኔ ያስተላለፈው ፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ነው፡፡ ውሳኔው የሚፈጸመው በአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤት በውክልና ነው፡፡ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ለማስፈጸም ሥልጣን የለውም፤›› በማለት ምላሽ ሰጥቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ በሰጠው ብይን እንዳብራራው፣ ኤጀንሲው ፍርድ ቤቱ ሥልጣን እንደሌለው ቢገልጽም ማስረጃ አላቀረበም፡፡ ኤጀንሲው ጊዜ እንደሚያስፈልገው ቢገልጽም፣ እንዲያስፈጽም ከስምንት ወራት በላይ ስለተሰጠው በቂ ጊዜ እንደሆነና በቤቱ ውስጥ የሚኖሩት ከፍተኛ ባለሥልጣን ናቸው የሚለው ተቀባይነት እንደሌለው በመዘርዘር፣ ቀደም ብሎ ሌተና ጄኔራል ፃድቃን ገብረ ትንሳዔ፣ በአሁኑ ጊዜ ደግሞ አቶ በረከት ስምዖን የሚኖሩበት መኖሪያ ቤት ለባለቤቱ አቶ መሐሪ ተወልደ ብርሃን እንዲያስረክብ፣ የቤቶች ኤጀንሲ ከፌዴራል ፍርድ ቤቶች ፍርድ አፈጻጸም ዳይሬክቶሬት ኅዳር 16 ቀን 2008 ዓ.ም. ትዕዛዝ ተላልፎለታል፡፡
የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀብታሙ ሲሳይ ለከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር በጻፉት ደብዳቤ፣ በቤቱ ውስጥ የሚኖሩትን ባለሥልጣን የሚመጥን ቤት ስላልተገኘ ለግለሰቡ የቤት ካሳና ተመጣጣኝ ቦታ እንዲሰጣቸው አመልክተዋል፡፡