በተለያዩ የስፖርት ዓይነቶች ላይ በመሳተፍ ለአገራቸው ድል ያመጡና ፈር ቀዳጅ የሆኑ ሴት ኢትዮጵያውያን የስፖርቱ አካላት የምሥጋና ሽልማት ተበረከተላቸው፡፡
ኢመልቱ ሚዲያ ከኢፌዴሪ ወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴና ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጋር በመተባበር ‹‹የኢትዮጵያ ስፖርትና የሴቶች ሚና›› ሲምፖዚየም ላይ ሽልማታቸውን ተረክበዋል፡፡
አትሌት ደራርቱ ቱሉ (ኮ/ል)፣ ፋጡማ ሮባ፣ አሠልጣኝ መሠረት ማኔ፣ ወ/ሮ ዳግማዊ ግርማይና ኢንተርናሽናል ዳኛ ሊዲያ ታፈሰ የምሥጋና ሽልማታቸውን ተረክበዋል፡፡ ወጣት ናርዶስ ሲሳይ በመላው አፍሪካ በወርልድ ቴኳንዶ የወርቅ ሜዳልያ ያስገኘች፣ በቮሊቮል ስፖርት ለረጅም ጊዜ ያሳለፈችው አሚና ሽኩር እንዲሁም በቦክስና በብስክሌት የራሳቸውን አስተዋጽኦ ያደረጉ አካላት የምሥጋና ሽልማቱ አባል ሆነዋል፡፡
በሲምፖዚየሙ የሴቶች ተሳትፎ በኦሊምፒክ፣ ሴቶች በስፖርት አመራር ውስጥ ያላቸው ሚናና የሚያጋጥማቸውን ችግሮች በማንሳት ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በውይይቱ ወቅት የቀረበው የመነሻ ጽሑፍን መንደርደሪያ በማድረግ ከተሳታፊዎች አስተያየትና ጥያቄ የተነሳ ሲሆን በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ውስጥ ሴት አመራሮች መካተት አለባቸው ተብሏል፡፡
ሴት አመራሮች በሁሉም የሥራ ደረጃ ላይ ይሳተፉ ሲባል የተቀመጠው ሕግን ለማሟላት ብቻ እንጂ በአግባቡ ሥልጣናቸውን እንዳይጠቀሙ ጫና ሲደረግባቸው ቆይቷል ተብሏል፡፡ በአንድ የስፖርት ዘርፍ ላይ በሴት አመራሮች ተብሎ የተመቀጠውን መብት ይልቅ በወንዶች የበላይነት በመዋጥ በራሳቸው ውሳኔ እንዳይፀኑ እንደሚያደርጋቸው ተጠቅሷል፡፡
የዕውቅና ሽልማት የተበረከተላትና በአፍሪካ የመጀመሪያዋ የወንድ እግር ኳስ ክለብ አሠልጣኝ መሠረት ማኔ ‹‹ሚኒስትር መሥሪያ ቤቱ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉትን ሴት ስፖርተኞች ጠንቅቀው ያውቋቸዋል ወይ?›› በማለት ጥያቄዋን አንስታለች፡፡ በተጨማሪም አሠልጣኟ ባለፈችበት የአሠልጣኝነት ዘመን ከፍተኛ ፈተናዎች እንዳጋጠሟትና በአሁኑ ወቅት ለሴት ስፖርተኞች የሚሰጠው ዝቅተኛ አመለካከት ትኩረት እንደሚሻ ጠቅሳለች፡፡ በሌላ በኩል በየስፖርት ፌዴሬሽኖች ሴት አመራሮችን ተሳታፊ እንዲሆኑ የሚመደብ የገንዘብ በጀት መኖሩን መንግሥትም የተበጀተው ገንዘብ በአግባቡ ሥራ ላይ መዋሉን ማረጋገጥ አለበት የሚል አስተያየት ተነስቷል፡፡ በአፍሪካ ዋንጫ ሁለት የጥሎ ማለፍና የሴቶች የ2019 የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ የዳኘችው ኢንተርናሽናል ሊዲያ ታፈሰ በበኩሏ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሥራዋን ማከናወን ብትችልም በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ላይ ለመዳኘት ዕድል ማጣቷን ተናግራለች፡፡ እነዚህን ትልልቅ ውድድሮች ስታከናውንም አንድም የእግር ኳስ ፌዴሬሽን አካል ምሥጋና እንዳልቸራትና ያለው ትኩረት አናሳ መሆኑን አስታውሳለች፡፡ የወንድ አመራሮች ላይ ብቻ ሳይሆን ችግሩ ያለው ሴቶችም የችግሩ መባባስ ምክንያት እንደሆኑ አክላለች፡፡
በመጨረሻም አዲሱ የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አሸብር ወልደጊዮርጊስ ሰላሳ በመቶ የሆኑትን አመራሮች ውስጥ ሴቶችን እንዳካተቱና በቀጣይም ቁጥሩን ከፍ ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡