Monday, September 25, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

የሲሚንቶ ገበያ ተቀዛቀዘ

ተዛማጅ ፅሁፎች

– የኤሌክትሪክ መቆራረጥ ለሲሚንቶ ፋብሪካዎች ፈተና መሆኑ ተነገረ

በኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ እየተፈተነ የሚገኘው የሲሚንቶ ኢንዱስትሪ የገበያ መቀዛቀዝ አሳየ፡፡ አገር ውስጥ የሚገኙ የሲሚንቶ ፋብሪካዎች ዓመታዊ የማምረት አቅማቸው 13 ሚሊዮን ኩንታል ቢሆንም፣ ሽያጩ ግን ከሰባት ሚሊዮን ኩንታል ያልበለጠ መሆኑ ታውቋል፡፡

ከገበያ መቀዛቀዝ ባሻገር የመንግሥት የልማት ድርጅት የሆነው ሙገር ሲሚንቶ፣ ሰሞኑን አንድ ኩንታል ፒፒሲ ሲሚንቶ የሚሸጥበትን ዋጋ ከ210 ብር ወደ 190 ብር አውርዶታል፡፡

በኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥና ከቀትር በኋላ 11፡00 ሰዓት እስከ ምሽት 4፡00 ሰዓት ድረስ ኃይል እንዳይጠቀሙ በመንግሥት ትዕዛዝ በመሰጠቱ የገበያ መቀዛቀዝ መፈጠሩ የተነገረ ሲሆን፣ የተለያዩ ሲሚንቶ ፋብሪካዎችም ሥራ እያቆሙ ነው፡፡

ሥራ ካቆሙ ፋብሪካዎች ውስጥ ሲኤች ክሊንከር፣ ሁዎንግሽን ሲሚንቶና ኢስት ሲሚንቶ ይገኙበታል፡፡ የኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን ተጠባባቂ ዋና ዳይሬክተር አቶ መኮንን ዘርጋው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ለሲሚንቶ ፋብሪካዎች ትልቁ ፈተና ሆኗል፡፡

የሲሚንቶ ፋብሪካዎች ከአንድ ሺሕ ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ በላይ ሙቀት ስለሚፈልጉ፣ ይህ ሙቀት ከተፈጠረ በኋላ ኃይል ሲቋረጥ በርካታ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች ለብልሽት እንደሚዳረጉ፣ እንደገና ኃይል ሲመጣ ደግሞ ፋብሪካዎቹን ወደ ሥራ ለመመለስ አስቸጋሪ እንደሆነ አቶ መኮንን ገልጸዋል፡፡

የገበያውን መቀዛቀዝ በተመለከተ ሁሌም በክረምት ወራትና ክረምት ከወጣ በኋላ ለተወሰኑ ወራት የሲሚንቶ ገበያ መቀዛቀዙ የተለመደ እንደሆነና ከመብራት ጋር እንደማይገናኝ ገልጸዋል፡፡ ይሁንና በዚህ ሐሳብ የማይስማሙ አሉ፡፡

ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የአንድ ሲሚንቶ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ መንግሥት በአንድ ጊዜ በርካታ ፕሮጀክቶችን ያስጀመረ በመሆኑ፣ ለሚያሠራው ሥራ ክፍያ ለመፈጸም እየተቸገረ ነው፡፡

መንግሥት የበጀት እጥረት ስላለበት መንግሥት ክፍያ እየፈጸመ ባለመሆኑ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪው በመቀዛቀዙ የሲሚንቶ ገበያውም ሊቀዛቀዝ እንደቻለ አመልክተዋል፡፡ ባለፉት በርካታ ዓመታት የዋጋ ንረት ሲያጋጥመው የቆየው የሲሚንቶ ገበያ፣ በአሁኑ ጊዜ መቀዛቀዝ ስለታየበት፣ ሁሉም የሲሚንቶ ፋብሪካዎች ከ190 ብር እስከ 210 ብር ድረስ ባለው ዋጋ በመሸጥ ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ቀደም ባሉት ጊዜያት ሲሚንቶ ገበያው ውስጥ በኩንታል እስከ 400 ብር ይሸጥ ነበር፡፡

አቶ መኮንን ሙገር የሲሚንቶ ዋጋ ሊቀነስ ከቻለባቸው ምክንያቶች አንዱ ሲጠቀም የቆየውን ጥቁር ናፍጣ ትቶ፣ በድንጋይ ከሰል እንዲጠቀም በመወሰኑ ነው ብለዋል፡፡

በ15 ቀናት ውስጥ በድንጋይ ከሰል መጠቀም እንደሚጀምር የተናገሩት አቶ መኮንን፣ ከጥቁር ናፍጣ ይልቅ የድንጋይ ከሰል ርካሽ በመሆኑ ሙገር ዋጋ ለመቀነሱ አንዱ ምክንያት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች