የፋሲካ እንቁላል ይሉታል፡፡ በፋሲካ ወቅት በቀለም ተውቦ፤ ተጋጊጦና ተነቅሶም ለወዳጅ ዘመድ እንደ ስጦታ የሚቀርብ ነው፡፡ በምእራባውያኑ በዕድሜ ጠገቡ ባህል የዶሮን እንቁላል በቀለማት አስውቦ ለወዳጅ የሚበረከትበት አካሄድ ቢኖርም በዘመናዊው ባህል ደግሞ ከቸኮሌት የተሠራ እንቁላልን በባለቀለማት መጠቅለያ በመጠቅለል ወይም ከላስቲክ የተሠራ እንቁላልን በቸኮሌት በመሙላት ስጦታ ሲለዋወጡም እየተስተዋለ ነው፡፡
በክርስትና ባህል እንቁላል የሚገለጸው ከመልሶ መወለድና ለምነት ጋር ቢሆንም ከፋሲካ ጋር በተያያዘ ግን እንቁላል የሚገለጸው የኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ባዶ ሆኖ መገኘትን ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም እንቁላሉ በቀይ ቀለም የሚዋበውም ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ልጆችን ለማዳን ሲል ያፈሰሰውን ደም ለማስታወስ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ባህል በሜሶፖታሚያ ክርስትና ከገባበት ጊዜ አንስቶ እንደተጀመረ ይነገራል፡፡ በኋላም ወደ ሩሲያና ሰርቢያ በኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አማካይነት ገብቷል፡፡ በመቀጠልም በካቶሊክና በፕሮቴስታንት ቤተ ክርስቲያናት አማካይነት ወደ አውሮፓ ዘልቋል፡፡ በኢትዮጵያ ለፋሲካ በዓል በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ ዶሮ ማረድና አክፍሎት ማድረግ የተለመደ ነው፡፡