የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በየወሩ መሬት በሊዝ ለማስተላለፍ ጨረታ እንደሚያወጣ ቢደነግግም፣ ላለፉት ሰባት ወራት አንድም ጊዜ ጨረታ አላወጣም፡፡ የአዲስ አበባ መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ጨረታ ማውጣት ያልቻለው፣ ጨረታውን ግልጽ ለማድረግ ዘመናዊ አሠራር ተግባራዊ ማድረግ በማስፈለጉ ነው ብሏል፡፡ ለዚህም ሲባል አዲስ ሶፍትዌር እየተዘጋጀ መሆኑ ታውቋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ሥር የሚገኘው የመሬት ባንክና ማስተላለፍ ጽሕፈት ቤት፣ ለመጨረሻ ጊዜ የመሬት ሊዝ ጨረታ ያወጣው ባለፈው ዓመት ነሐሴ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ነበር፡፡
ከ28ኛው ሊዝ ጨረታ በኋላ በወሩ 29ኛው ሊዝ ጨረታ ይወጣል ተብሎ ቢጠበቅም፣ ጨረታው ሳይወጣ በመጋቢት ሰባተኛ ወሩ ተጠናቋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሀርጋሞ ሃማም ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ 29ኛው የሊዝ ጨረታ በቅርቡ ይወጣል፡፡
‹‹እስካሁን ጨረታውን ማውጣት ያልተቻለው አሠራሩን ግልጽ ለማድረግ አዲስ ሶፍትዌር ማልማት በማስፈለጉ ነው፡፡ የአዲሱ ሶፍትዌር ሥራ በመጠናቀቁ በቅርቡ ጨረታው ይወጣል፤›› ብለዋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ የሚወጡ የመሬት ሊዝ ጨረታዎች ይፋ ከሆኑ በኋላ ማሻሻያ የሚደረግላቸው ሲሆን፣ ከዚያም ባለፈ በጥቃቅን ጉዳዮች ይሰረዙም ነበር፡፡
የ28ኛው ሊዝ ጨረታ በወጣበት ጊዜ እንኳን 36 ቦታዎች የተሰረዙ ሲሆን፣ ጨረታውን ያሸነፉ ደግሞ በመሰረዙ ከፍተኛ ቅሬታ ሲያሰሙ ቆይተዋል፡፡
አቶ ሀርጋሞ እንዳሉት፣ እነዚህ ቦታዎች በመሰረዛቸው የከተማው አስተዳደር ያወጣው ወጪም ባክኗል፡፡ ቅሬታዎች ከተሰሙም በኋላ አስተዳደሩ ግምገማ በማካሄድ፣ ቦታዎቹ መሰረዛቸው ለቅሬታ መሰማት ምክንያት መሆኑን አምኗል ብለዋል፡፡
ቢሮው ከዚህ ቀደም የነበሩ ችግሮችን በመፍታት 102 ቦታዎችን አዘጋጅቶ ለአልሚዎች ለማስተላለፍ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታውቋል፡፡