ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ ሳያገኙ፣ ዘንድሮ መካሄድ የነበረበት የአዲስ አበባና የድሬዳዋ ከተማ ምክር ቤቶችና የአካባቢ ምርጫ ለ2011 ዓ.ም. በአብላጫ ድምፅ ተላለፈ።
ምክር ቤቱ ዛሬ መጋቢት 4 ቀን 2010 ዓ.ም. ባካሄደው ስብሰባ በምርጫው መራዘም ላይ ከተሟገተ በኋላ በስምንት ድምፀ ተአቅቦ በአብላጫ ድምፅ አፅድቆታል።
ጥያቄ ያቀረቡ የምክር ቤቱ አባላት ሕገ መንግሥቱም ሆነ የክልል መንግሥታት ሕጎች ምርጫ በየአምስት ዓመቱ እንደሚደረጉ መደንገጋቸውን በመጥቀስ፣ ምርጫው እንዲራዘም የቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ከዚህ አንፃር እንዲታይላቸው ጠይቀዋል።
‹‹ምርጫው ሲራዘም የምርጫ ዘመናቸውን ያጠናቀቁ የምክር ቤት አባላት የሥራ ዘመንና ሥልጣንም አብሮ ይራዘማል ወይ?›› የሚል ጥያቄም በሌላ አባል ቀርቧል፡፡
ምርጫው እንዲራዘምለት የውሳኔ ሐሳብ ያቀረበው የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሲሆን፣ ከፀጥታ ጋር በተያያዙ ችግሮች ነው ምርጫው ለ2011 ዓ.ም. እንዲተላለፍለት ፓርላማውን የጠየቀው። ይሁን እንጂ በርካታ የምክር ቤቱ አባላት ‹‹በ2011 ዓ.ም. በየትኛው ወር?›› የሚለው የጊዜ ወሰን መቀመጥ ይኖርበታል ሲሉ ተሟግተዋል። ‹‹ጊዜው ካልተቀመጠ በነሐሴ ወርም ሊሆን ይችላል፤ ይኼ ደግሞ ቦርዱ በ2012 ዓ.ም. ለሚያካሂደው አገር አቀፍ ምርጫ የዝግጅት ጊዜውን ይሻማበታል፤›› የሚል መከራከሪያ የፓርላማ አባላቱ አቅርበዋል።
በቀረበው የውሳኔ ሐሳብ ላይ ምርጫው ለ2011 ዓ.ም. እንዲራዘም እንጂ የሚካሄድበት ወር ባለመጠቀሱ፣ እንደተጠየቀው ቢፀድቅ ይሻላል የሚል ሐሳብ ስብሰባውን በመሩት የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባዔ ወ/ሮ ሽታዬ ምናለ ቀርቧል። ይሁን እንጂ ሐሳቡ ወዲያውኑ ተቀባይነት አላገኘም። ‹‹የጊዜ ገደቡ የግድ በውሳኔ ሐሳቡ ላይ ባይቀመጥም፣ ይኼንን ስብሰባ ለሌላ ጊዜ አስተላለፈን ተስተካክሎ እንዲመጣ ይደረግ፤›› ሲሉ አንድ የምክር ቤት አባል ሐሳብ አቅርበው ነበር።
በፓርላማው የመንግሥት ረዳታ ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አማኑኤል አብርሃም ምርጫው ከመስከረም እስከ ታኅሳስ 30 ቀን 2011 ዓ.ም. እንደሚካሄድ መረጃ የሰጡ ቢሆንም፣ ምክትል አፈ ጉባዔዋ አልተቀበሉትም። ምርጫው እንዲራዘም የተጠየቀውም በምርጫ ቦርድ ማቋቋሚያ አዋጅ መሠረት በመሆኑ የሕግ መጣረስ እንደሌለውና የምርጫ ዘመናቸውን የጨረሱ ተመራጮች የሥራ ዘመን መራዘምን አስመልክቶ የቀረበው ጥያቄ ከአጀንዳ ውጪ እንደሆነ በመጠቆም ወደ ድምፅ መስጠት ተገብቷል።
በዚህም መሠረት የውሳኔ ሐሳቡ በስምንት ድምፀ ተአቅቦ በአብላጫ ድምፅ ፀድቋል። ምርጫ ቦርድ ምርጫው እንዲራዘምለት የጠየቀው በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍሎች ተፈጥሮ የነበረው የፀጥታ ችግር የምርጫ ዝግጅቱ የተማሏ እንዳይሆን እንዳደረገበትና በዚህም የተነሳ ምርጫውን በተያዘለት ጊዜ ማካሄድ እንደማይቻል በመግለጽ ነው።
በአሁኑ ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለስድስት ወራት በመታወጁ ምክንያት፣ በሕገ መንግሥቱ የሠፈሩ መብቶች በአዋጁ ስለሚገደቡ ምርጫ ለማካሄድ አስቸጋሪ እንደሚሆን የሕግ ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡