ከሳምንት በፊት ባለመግባባት የተጠናቀቀውን ኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ የሚያደርጉትን ድርድር ለማስቀጠል፣ ግብፅ ተጨማሪ ዙር የድርድር ዕድል እንዲሰጣት ጠየቀች፡፡
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሜህ ሽኩሪ ለግብፅ መገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት፣ በተያዘው ሳምንት መጨረሻ አካባቢ ሦስቱ አገሮች በህዳሴ ግድቡ ላይ ተጨማሪ ድርድር በግብፅ ካይሮ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በዚህኛው የህዳሴ ግድብ ውይይት ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች፣ የውኃ ጉዳይ ሚኒስትሮችና የደኅንነት ኃላፊዎች ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ ማቅረባቸው ተሰምቷል፡፡
ከኢትዮጵያ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ሪፖርተር እንዳረጋገጠው፣ ጥያቄው መቅረቡንና በኢትዮጵያ በኩል ለማንኛውም ውይይት ዝግጅት መኖሩ ተገልጿል፡፡ ይሁን እንጂ የግብፅ መንግሥት ተደራዳሪዎች በህዳሴው ግድብ ላይ የሚካሄደው ውይይት ውጤት እንዳያመጣ የማደናቀፍ ተግባር እንደሚያከናውኑ፣ የኢትዮጵያና የሱዳን ባለሥልጣናት ይከሳሉ፡፡
የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም ከሳምንት በፊት በሱዳን ካርቱም የተካሄደው ድርድር ውጤት አልባ የሆነው፣ ግብፅ ኢትዮጵያ ያልፈረመችበትን እ.ኤ.አ. የ1959 የቅኝ ግዛት የውኃ ክፍፍል ስምምነት እንዲከበርላት በመጠየቋ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አህመድ አቡ ዘይድ ደግሞ፣ አገራቸው የካርቱሙን ድርድር አደናቅፋለች መባሉን አስተባብለዋል፡፡ እሳቸው ይህንን ይበሉ እንጂ የግብፅ ተደራዳሪዎች በየስብሰባው ይዘውት የሚቀርቡት ሐሳብ ኢትዮጵያና ሱዳንን እንደማያስደስት ብዙ ጊዜ ተዘግቧል፡፡
ግብፅ ይህንን ጥያቄ በተደጋጋሚ ጊዜ ስታነሳና በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ ጥያቄው ውድቅ ሲደረግ መቆየቱን፣ ነገር ግን አሁንም ጥያቄው መቀጠሉ ስብሰባውን ውጤት አልባ የማድረግ እንቅስቃሴ መሆኑን አንድ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የኢትዮጵያ ተደራዳሪ ቡድን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ይህ ዓይነቱ ድርድር የአገሮች ጥቅም የሚከበርበት በመሆኑ እልህ እንደሚያስጨርስም ጠቁመዋል፡፡ ሦስቱ አገሮች በአሁኑ ወቅት ለመፍታት የሚፈልጉት ችግር የህዳሴ ግድቡ ውኃ አሞላልና አለቃቀቅን በተመለከተ ነው፡፡