አሠልጣኝ አልባው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ) በፊፋ ወርኃዊ ደረጃ ስምንት ደረጃዎችን በመጣል ከ137ኛ ወደ 145ኛ ዝቅ ማለቱ ባለፈው ሐሙስ ተገልጿል፡፡
ባለፉት ወራት ምንም ዓይነት ግጥሚያ የወዳጅነትን ጨምሮ ያላደረጉት ዋሊያዎቹ ለደረጃቸው ማሽቆልቆል በምክንያትነት ይነሳል፡፡
ኦል አፍሪካ እንደዘገበው፣ በዘንድሮው የሩሲያ የዓለም ዋንጫ የአፍሪካ ተወካይ ከሆኑት አገሮች ቱኒዚያ አስደናቂ ዕመርታን ያሳየችው ከ23ኛነት ወደ 14ኛነት ከፍ በማለት ነው፡፡ ሴኔጋል 28ኛ፣ ሞሮኮ ባለችበት 42ኛ፣ ግብፅ 46ኛ ሲሆኑ ባለፈው ወር 52ኛ የነበረችው ከመጀመርያዎቹ ምርጥ 50ዎቹ ውስጥ ለመግባት ያስቻላትን ተቆናጣለች፡፡
የዓለም ሻምፒዮኗ ጀርመን ቁንጮነቷን ስትቀጥል የአምስት ጊዜ የዓለም ሻምፒዮናዋ ብራዚል በሁለተኛነቷ ፀንታለች፡፡ ባለፈው ወር ሳዑዲ ዓረቢያን 4 ለ0 የረታችው ቤልጂየም ሦስተኝነቱን፣ የአውሮፓ ሻምፒዮኗ ፖርቱጋል አራተኛነቱን፣ አርጀንቲና አምስተኛነቱን ይዘዋል፡፡
ኢትዮጵያ በምትገኝበት የምሥራቅና መካከለኛው አፍሪካ (ሴካፋ) ዞን ዑጋንዳ መሪነቱን አላስነካችም፤ 75ኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ፣ የዞኑ ሻምፒዮኗ ኬንያ ሁለተኛ ያሰኛትን 113ኛ ደረጃን፣ የለጠቀችው ሩዋንዳ 123ኛ ላይ ተቀምጠዋል፡፡ ሱዳን (126ኛ)፣ ታንዛኒያ (137ኛ)፣ ኢትዮጵያና ቡሩንዲ በጋራ 145ኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
ቀጣዩ የፊፋ የዓለም ደረጃ ይፋ የሚደረገው ግንቦት 9 ቀን የሩሲያው የዓለም ዋንጫ ሰኔ 7 ቀን ከመጀመሩ በፊት መሆኑ ታውቋል፡፡