ካለፉት አራት ወራት ወዲህ በበቆሎ ላይ የታየው የአሜሪካ መጤ ተምች በአገሪቱ መጀመርያ ከታየበት ከደቡብ ጀምሮ አማራ፣ ኦሮሚያ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ፣ ጋምቤላና ትግራይ ክልሎች በ135 ሺሕ ሔክታር መሬት ላይ የተዘራ በቆሎ ማጥቃቱ ተገለጸ፡፡ በክልሎቹ ከተዘራው አንድ ሚሊዮን ሔክታር በቆሎ ውስጥ ሙሉ ለሙሉ የወደመ እንደሌለም ተጠቁሟል፡፡
የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ሚኒስቴር የእርሻ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተስፋዬ መንግሥቴ፣ በመኸር እርሻ እንቅስቃሴና በወቅታዊው የአሜሪካ ተምች ላይ ዓርብ ሰኔ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ፣ ለኢትዮጵያም ሆነ ለአገሪቱ ባለሙያዎች አዲስ የሆነው የአሜሪካ ተምች ለግብርናው ዘርፍ ከባድ ፈተና መሆኑንና በበቆሎ ከተሸፈነው እርሻ በ135 ሺሕ ሔክታር መሬት ላይ መታየቱን አስረድተዋል፡፡
በባህላዊና በኬሚካል በተደረገው መከላከል 83 ሺሕ ሔክታር ማሳ ከተምቹ መከላከል መቻሉን፣ ከዚህ ውስጥ 43 በመቶው በባህላዊ የመከላከል መንገድ መከናወኑንና አብዛኛው መከላከል በባህላዊ መንገድ መሆን አለበት ተብሎ እንደ መርህ መወሰዱን አስታውሰዋል፡፡
አንዳንድ ክልሎች 75 በመቶ ባህላዊ አሠራር 25 በመቶ የኬሚካል ርጭት እንደሚጠቀሙና ይኼንንም ደቡብ ክልል ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
ሆኖም በኬሚካል መከላከሉ ላይ የማዘንበል ልማድ መኖሩ ትልቅ ክፍተት እንደሆነ፣ ከዚህ አኴያ በኬሚካል መጠቀምን ማስወገድ እንደሚገባና የመጨረሻ አማራጭ መሆን እንዳለበት አክለዋል፡፡
በሥነ ምኅዳርና በሰዎች ላይ ካለው አሉታዊ ተፅዕኖ አንፃር ኬሚካል እንደማይመከር በመግለጽ፣ ተምቹ ኬሚካሉን ከተላመደ ወደፊት አደጋውን መቋቋም ከማይቻልበት ደረጃ እንደሚደረስ ተናግረዋል፡፡ ‹‹ኬሚካል በመቀነስ ባህላዊ ትግበራ ላይ ማተኮር ስለሚያስፈልግም ይኼንኑ ለማስፈን እየተሠራ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የአሜሪካ ተምችን በለቀማ ለማጥፋት ኅብረተሰቡን ማሳተፍ የተጀመረ ቢሆንም በኅብረተሰብ ንቅናቄ ላይ ክፍተት እንዳለ፣ ተምቹን በአርሶ አደሩና በቤተሰቡ ብቻ መከላከል እንደማይቻልና ችግሩን ለመቆጣጠር ዘመቻ እንደሚኖር ጠቁመዋል፡፡
ተምቹ በኢትዮጵያ ከመከሰቱ አስቀድሞ ናይጄሪያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ታንዛኒያና ኬንያ ሲገባ ወደ ኢትዮጵያ ሊገባ ይችላል ተብሎ ለአገሪቱና ለባለሙያዎቿ እንግዳ በመሆኑ መረጃ ለማቀናጀት፣ በምርምር ተቋማትና በሚመለከታቸው አካላት ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ነበር፡፡ ሆኖም መረጃ ተሰብስቦ ለአርሶ አደሩና ለባለሙያዎች ሥልጠና ለመስጠት እየተዘጋጁ ባሉበት ወቅት፣ በደቡብ ክልል በቤንች ማጂ ዞን ተምቹ ቀድሞ መታየቱን ሚኒስትር ዴኤታው አስረድተዋል፡፡
አንድ ሔክታር መሬት በመስመር የተዘራ 58 ሺሕ ያህል የበቆሎ እግር ሲይዝ፣ ከዘር ጀምሮ እስከ ማንሳት ድረስም አርሶ አደሩን እስከ 15 ሺሕ ብር ያስወጣዋል፡፡ ከአንድ ሔክታር መሬት በአማካይ ከ40 እስከ 50 ኩንታል በቆሎ ሲገኝ፣ ሞዴሎች ደግሞ ከዚህ በላይ ያገኛሉ ይባላል፡፡ አነስተኛ አርሶ አደሮች ደግሞ በሔክታር ከ20 እስከ 30 ኩንታል እንደሚያገኙ፣ የጉራጌ ዞን የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ባለሙያዎች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡