በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን አማካይነት በየዓመቱ በሚዘጋጀውና ዘንድሮም እየተካሔደ በሚገኝ የኮንፌደሬሽን ዋንጫ ውድድር ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው ወላይታ ዲቻ፣ ረቡዕ ሚያዝያ 10 ቀን 2010 ዓ.ም. በሐዋሳ ስታዲየም በሚያደርገው ጨዋታ ወደ ቀጣይ ዙር የማለፍ ዕድሉ ይለይለታል፡፡
በመጀመርያው ዙር ውድድር በታንዛኒያው ያንግ አፍሪካ ክለብ 2 ለ 0 የተረታው ወላይታ ዲቻ፣ በሐዋሳ ስታዲየም የሚያደርገው ጨዋታ ወደ ቀጣዩ ዙር የማለፍ ዕድሉን ይወስናል፡፡
በታሪኩ በአኅጉራዊ ውድድሮች ሲሳተፍ የመጀመርያው በሆነው በኮንፌደሬሽን ዋንጫ የክለቦች ውድድር ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ ለሚወስነውና በሜዳው ለሚያደርገው ጨዋታ ትልቅ ግምት ተሰጥቶታል፡፡ ወላይታ ዲቻዎች በቅድመ ማጣሪያ ጨዋታቸው የዛንዚባሩን ዚማሞቶ ክለብ በድምር ውጤት 2 ለ 1 በመርታት፣ እንዲሁም የግብፁን ዛማሊክ በፍፁም ቅጣት ምት አጠቃላይ ውጤት 4 ለ 3 በመርታት ለአሁኑ ዙር መድረሳቸው ይታወቃል፡፡ ወደ ምድብ ድልድል ለመግባት የዛሬውን ጨዋታ ግብ ሳይቆጠርባቸው፣ እንዲሁም ከሁለት ጎል በላይ በማስቆጠር ማሸነፍ ይጠበቅባቸዋል፡፡
በሜዳቸው በቀላሉ ያለ መረታት ልማድ ያላቸው ወላይታ ዲቻዎች፣ በሐዋሳ ስታዲየም በርካታ ቁጥር ያለው ተመልካች እንተለመደው ከፍተኛ ድጋፉን እንደሚሰጣቸው ይጠበቃል፡፡
በሌላ በኩል የኮንጎ ብራዚቫሉን ካራ ብራዛቭሊን 1 ለ 0 የረታው ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ወደ ኮንጎ በማቅናት የመልስ ጨዋታውን ረቡዕ ሚያዝያ 10 ቀን 2010 ዓ.ም. በተመሳሳይ ያካሂዳል፡፡
ከአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎው ቢሰናበትም፣ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ መሳተፍ የቻለው ቅዱስ ጊዮርጊስ ውጤቱን አስጠብቆ ወደ ተከታዩ ዙር ለማለፍ የተሻለ ዕድል እንዳለው ይገመታል፡፡