– ባለፈው ዓርብ እስከረፋዱ ድረስ የባቡር ትራንስፖርት አልነበረም
የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ የአዲስ አበባ ቀላል የኤሌክትሪክ ባቡር አገልግሎቱን በአግባቡ እንዳይሰጥ እያስተጓጐለው መሆኑ ተጠቆመ፡፡
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር የትራንስፖርት አገልግሎት ከመጀመሩ በፊት፣ ይህንኑ የአዲስ አበባ ከተማ የኃይል አቅርቦት መቆራረጥ ከግምት ውስጥ በማስገባት የባቡር ትራንስፖርቱ የኃይል ምንጩን ከብሔራዊ የኤሌክትሪክ ቋት እንዲያገኝ አድርጓል፡፡ ይህም ማለት አዲስ አበባ ውስጥ የኃይል መቆራረጥ ቢኖር እንኳን የባቡሩ ትራንስፖርቱ አገልግሎቱን መስጠት ያስችለዋል ተብሎ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ከሁለት ሳምንት በፊት በመላ አገሪቱ በተከሰተ የኃይል መቋረጥ ምክንያት የባቡሩ ትራንስፖርት ተስተጓጉሎ ነበር፡፡
በተመሳሳይ ባለፈው ዓርብ ታህሳስ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ የባቡር ትራንስፖርቱ በአጠቃላይ አገልግሎቱን መስጠት የጀመረው ከረፋዱ አራት ሰዓት አካባቢ መሆኑን፣ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አወቀ ሙሉ አረጋግጠዋል፡፡
‹‹የኃይል አቅርቦት ዛሬም በመቋረጡ እስከ ረፋዱ ድረስ አገልግሎት መስጠት አልተቻለም፡፡ ይህ ሁኔታ አሉታዊ ተፅዕኖ አለው፡፡ በዚህ ሁኔታ የሚቀጥል ከሆነ አማራጭ ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡
የኃይል አቅርቦት ሲቋረጥ ባቡሮቹ ባሉበት የሚቆሙ መሆኑን፣ ነገር ግን የባቡሮቹ በሮች የሚከፈቱ ስለሆነ ተሳፋሪዎች መውረድ እንደማይቸገሩ አቶ አወቀ ገልጸዋል፡፡
እንደዚህ ዓይነት ችግር በሚያጋጥምበት ወቅት የተሳፋሪዎች ትኬት ላይ ምልክት በማድረግ በሌላ ቀን እንዲገለገሉበት የሚደረግ መሆኑን አቶ አወቀ ተናግረው፣ ችግሩ ቢቀጥል ሊወሰዱ ስለሚችሉ አማራጮች ግን የገለጹት ነገር የለም፡፡
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ጌታቸው በትሩ ቀደም ሲል ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ ለቀረበላቸው ተመሳሳይ ጥያቄ አማራጩ በናፍጣ በሚሠራ ሎኮሞቲቭ በመጐተት አገልግሎት መስጠት መሆኑን ገልጸው ነበር፡፡