የጂቡቲ መንግሥት ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ዕቃዎች በዘመናዊ መሣሪያ በመፈተሽ በአንድ ኮንቴይነር ዕቃ፣ ከአሥር እስከ 35 ዶላር ለማስከፈል አዲስ ዕቅድ አወጣ፡፡
የጂቡቲ ወደብ አስተዳደር አዲሱን ክፍያ እ.ኤ.አ. ከጥር 15 ቀን 2016 ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚያደርግ፣ ለኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን ማሳወቁን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ይህ አዲስ አሠራር 85 በመቶ የሚሆነውን የወጪና ገቢ ንግድ በጂቡቲ ወደብ በኩል ለምትጠቀመው ኢትዮጵያ ዱብ ዕዳ ሆኗል፡፡
ባለፈው ዓርብ ታኅሳስ 1 ቀን 2008 ዓ.ም. ይህ መረጃ ለኢትዮጵያ መንግሥት እንደደረሰ፣ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስተባባሪነት ከጂቡቲ መንግሥት ጋር በጉዳዩ ላይ ለመወያየት እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡
የኢትዮጵያ ባህር ትራንስወደብና ሎጂስቲክስ ኢንተርፕራይዝ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቺፍ ኢንጂነር ዓለሙ አምባዬ ባለፈው ዓርብ ምሽት ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ ጉዳዩን ከአንድ ሰዓት በፊት መስማታቸውን ገልጸው፤ ከማሪታይም ባለሥልጣን ጋር ከተነጋገሩ በኋላ ማብራሪያ እንደሚሰጡ አስታውቀዋል፡፡
የማሪታይም ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መኰንን አበራ አስተያየት እንዲሰጡ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡ አዲሱ ክፍያ የውጭ ዕቃዎችን ይመለከት እንደሆነ የንግድ ሚኒስቴር የኤክስወደብ ፕሮሞሽን ዳይሬክተር ጄኔራል አቶ አሰፋ ሙሉጌታ ይህንን ጉዳይ እንዳልሰሙ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች እንደገለጹት፣ የጂቡቲ ወደብ አስተዳደር የመፈተሽ አቅሙን ለማሳደግ ከዚህ በፊት ከነበረው ልማዳዊ አሠራር (ማንዋል) ወደ ዘመናዊ (ዲጂታል) የፍተሻ ዘዴ ለመሸጋገር ሲሠራ ቆይቷል፡፡
በልማዳዊው የቀድሞ አሠራር ለፍተሻ ክፍያ አይጠይቅም ነበር፡፡ እ.ኤ.አ. ጥር 15 ቀን 2016 በሚጀመረው ዘመናዊ ፍተሻ ግን ክፍያ እንደሚጠይቅ፣ የጂቡቲ ወደብ አስተዳደር ለኢትዮጵያ አስታውቋል፡፡
የሎጂስቲክስ ኢንተርፕራይዝ ምንጮች እንደተናገሩት፣ ይህ ክፍያ በፍፁም ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም፡፡ ይህ ያልተጠበቀ ክፍያ ከተጀመረ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከመፈተኑ ባሻገር የኑሮ ውድነቱን እጅግ ያባብሳል ይላሉ፡፡
‹‹በኮንቴይነር ክፍያ የፈጸመ ነጋዴ ላወጣው ወጪ ክፍያ የሚጠይቀው ኅብረተሰቡን ነው፤›› በማለት የሚናገሩት የኢንተርፕራይዙ ምንጮች፣ አገሪቱንም ተጨማሪ የውጭ ምንዛሪ ያስወጣታል በማለት አዲሱ የጂቡቲ መንግሥት ተጨማሪ ክፍያ ጥያቄ፣ አገሪቱን ለውስብስብ ችግር እንደሚዳርግ አበክረው ገልጸዋል፡፡
ጂቡቲ ተጨማሪ ገቢ የሚገኝበትን አዲስ አሠራር ለመጀመር መዘጋጀቷን የሰሙ የኢትዮጵያ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ በዚህ ያልተጠበቀ የጂቡቲ መንግሥት ዕርምጃ በመደናገጥ የጂቡቲን መንግሥት ሐሳብ ለማስለወጥ ንግግር ለመጀመር ተዘጋጅተዋል ተብሏል፡፡