ከአምና ጀምሮ በዓለም ዙሪያ ትልቅ መነጋገሪያ ሆኖ ለወራት ያህል የዘለቀው የዓለም አቀፍ እግር ኳስ ማኅበር (ፊፋ) እና የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር (ዩኢኤፍኤ) ፕሬዚዳንቶች የሙስና ቅሌት በእገዳ ተጠናቋል፡፡ የፊፋም ሆነ የዩኢኤፍኤ ፕሬዚዳንቶች ውሳኔውን እንደማይቀበሉ ይልቁንም ጉዳዩን ወደ ዓለም አቀፍ የስፖርት ግልግል ፍርድ ቤት (ካስ) እንደሚወስዱት እየተናገሩ ይገኛል፡፡
ፊፋ ከትናንት በስቲያ ሰኞ ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት፣ ሁለቱ የእግር ኳስ አመራሮች 90 ቀን ጊዜያዊ እገዳ ተላልፎባቸው እንዲቆዩ በተደረገ በቀናት ውስጥ ከማንኛውም እግር ኳሳዊ እንቅስቃሴ ለስምንት ዓመት የታገዱ ስለመሆኑ ይፋ ሆኗል፡፡
የሴፕ ብላተርም ሆነ የሚሼል ፕላቲኒን የኃላፊነት ዘመንና የአሠራር ሁኔታን ሲከታተል የቆው በመጨረሻም በተለይ በፊፋ ቤት ተንስራፍቶ የቆየውን የሙስና ቅሌት በማጋለጥ ጭምር የአንበሳውን ድርሻ መውሰዱ የሚነገርለት ቢቢሲ፣ ሁለቱ የማኅበሩ አመራሮች ለሦስት ወራት ከተጣለባቸው እገዳ በተጨማሪ ሲያከናውን በቆየው የምርመራ ጋዜጠኝነት እ.ኤ.አ. በ2011 ፊፋ ለአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ሁለት ሚሊዮን ዶላር ያለ ምንም ምክንያት የከፈለ መሆኑን ማጋለጡ አይዘነጋም፡፡
ላለፉት 17 ዓመታት ፊፋን በፕሬዚዳንትነት እያስተዳደሩ የቆዩት የ79 ዓመቱ ስዊዘርላንዳዊው ሴፕ ፕላተርና ፈረንሳዊው ሚሼል ፕላቲኒ ባላቸው የጥቅም ትስስር እገዳው ባይተላለፍባቸው ኖሮ ፈረንሳዊው ፕላቲኒ የአዛውንቱን ወንበር ሊረከቡ የሚችሉበት እድል እንደነበራቸውም ከሙስናው ቅሌት ጎን ለጎን በሰፊው ሲነገር ነበረ፡፡
ከ2002 ጀምሮ የአውሮፓን እግር ኳስ መምራት የጀመሩት ፕላቲኒ የፊፋን ውሳኔ ተከትሎ፣ ‹‹እውነትነት በሌለው መሠረተ ቢስ ውንጀላ በእግር ኳሱ ዓለም የነበረኝን መልካም ሰብእና ለማጉደፍ የተጠነሰሰ ሴራ›› በማለት አሁንም ውሳኔውን እንደማይቀበሉት ነው ያስታወቁት፡፡ አዛውንቱ ሴፕ ብላተርም በተመሳሳይ ይህንኑ ውሳኔ ለዓለም አቀፍ የስፖርት ግልግል ፍርድ ቤት (ካስ) በመውስድ ለመብታቸው እንደሚታገሉ ጭምር እየገለጹ ይገኛል፡፡
ከፊፋ ቅሌት ጋር በተያያዘ እየተከናወነ በሚገኘው ምርመራ እስካሁን 27 ከፍተኛ የፊፋ አመራሮች እገዳ ተላልፎባቸው ጉዳያቸው እየታየ መሆኑ ይታወቃል፡፡