በተለያዩ የውስጥና የውጭ ችግሮች ተግባራዊ ሳይሆን ከአንድ ዓመት በላይ ሲንከባለል የቆየው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የመዋቅር ለውጥ ትግበራ ዓርብ ታኅሣሥ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. ይፋ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ ቅርበት ያላቸው የሪፖርተር ምንጮች አረጋገጡ፡፡ ‹‹ሕዝባዊ መሠረት ያላቸው የስፖርት አደረጃጀቶች እንዲፈጠሩ በማድረግ የአገሪቱን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ማሳደግ የሚችሉ አሠራሮችን በመዘርጋት የዘርፉን አገልግሎት ማስፋት›› ለሚለው ትኩረት ሰጥቶ ሲንቀሳቀስ የቆየው ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ የአዳዲስ ሙያተኞች ቅጥር እንደሚያከናውን ጭምር እየተነገረለት ይገኛል፡፡
በአገሪቱ ቀደምት ከሆኑ የስፖርት አደረጃጀቶች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በተለይም በፌዴሬሽኑ ሁለት መምሪያዎች ቴክኒክና ልማት እንዲሁም የግዥ የፋይናንስ የንብረትና የሰው ሀብት አስተዳደር ተብለው የሚታወቁት ቋሚ መምሪያዎች ለሁለትና ከዚያም በላይ እንዲከፋፈሉ ተደርጎ ለእያንዳንዳዱ መምሪያ ኃላፊዎች የውስጥና የውጭ የሥራ ማስታወቂያዎችን በማውጣት የመዋቅርና የአሠራር ለውጥ ያደርጋልም ተብሏል፡፡
ቀደም ባሉት ዓመታት በፌዴሬሽኑ ቴክኒክና ልማት በሚል ተመስርቶ ሲንቀሳቀስ የቆየው መምሪያ፣ በአዲሱ አደረጃጀት ሦስት መምሪያ ተደርጎ ተከፋፍሏል፡፡ በዚሁ መሠረት አንደኛውና የመጀመሪያው አትሌቲክሱን ታሳቢ ያደረገ አገልግሎትና አቅርቦት፣ ሁለተኛው ሥልጠና፣ ምርምርና ጥናት ሲሆን፣ የመጨረሻው ደግሞ የተሳትፎና የውድድር የሥራ ሒደቶች ተብለው መከፋፈላቸው ታውቋል፡፡ አገልግሎትና አቅርቦት የሥራ ሒደት የሚመለከታቸው የኃላፊነት ድርሻዎች የማኅበራትን ማዘውተሪያ ሥፍራ፣ የአትሌቲክሱን ብቃት እንዲሁም የአትሌት ማናጀሮችና የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎችንና የውድድር ብቃት የሚሉትን ያካትታል፡፡ ሥልጠና፣ ምርምርና ጥናት ተብሎ የተዋቀረው የሥራ ሒደት ደግሞ ከአቅም ግንባታ ጋር የተያያዙ የአሠልጣኞችና ተያያዥነት ያላቸው ሙያተኞች እንዲሁም የአትሌቶችና የዳኞች ሥልጠናን የሚከታተልና የሚያስፈጽም ሲሆን፣ በዚህ የሥራ ሒደት ሥር በተለይም ጥናትና ምርምር በዋናነት የተቀመጠለት ግብ በአትሌቲክሱ የሚታዩ ክፍተቶችን እየፈተሸ፣ ከዓለም አቀፍ ሁኔታ ጋር እያገናዘበ ጠቃሚና የስፖርቱን የዕድገት ሚዛን የሚጠብቅና የሚያስፈጽም እንደሚሆንም ተነግሯል፡፡ ሦስተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው የተሳትፎና የውድድር ሥራ ሒደት ደግሞ፣ ስፖርቱን ሕዝባዊ መሠረት በማስያዝ ጤናማና ምርታማ ማኅበረሰብ ለመገንባት የኅብረተሰብ ንቅናቄ ተሳትፎና ውድድሮች ማለትም የአገር ውስጥ እንዲሁም አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የውድድር መድረኮችን በመከታተል ማከናወን ይችል ዘንድ የተቋቋመ ነው ተብሏል፡፡
ሌላው በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ቀድሞ በተገለጸው መሠረት በአንድ የሥራ ሒደት ታጭቆ መቆየቱ የተነገረለት የግዥ፣ የፋይናንስ፣ የንብረትና የሰው ኃይል አስተዳደር የሥራ ሒደት በአዲሱ አደረጃጀት ሁለት የሥራ ሒደት ተደርጎ መዋቀሩ ተነግሯል፡፡ በዚሁ መሠረትም ግዥና ፋይናንስ አንዱና የመጀመሪያው ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ንብረትና የሰው ሀብት በሚል እንዲደራጅ ተደርጓል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ በአዲስ መልክ ያዘጋጀው የመዋቅር ለውጥ እውን ይሆን ዘንድ በፌዴሬሽኑ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኢንጂነር መሰለ ኃይሌ የሚመራ የለውጥ አተገባበር ኮሚቴና ከራሱ ከፌዴሬሽኑ የተውጣጣ ደልዳይ ኮሚቴ በዋናነት ኃላፊነቱን ወስደው ሥራውን ሲያከናውን መቆየታቸውም ታውቋል፡፡ በሁለቱ ኮሚቴዎች አማካይነትም አዲሱ መዋቅራዊ ለውጥ ዓርብ ታኅሣሥ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በይፋ እንደሚገልጽ ጭምር የዜናው ምንጭ አስረድቷል፡፡
እንደ ዜናው ምንጭ ከሆነ፣ በፌዴሬሽኑ አቅም አላቸው ተብሎ የታመነባቸው ባለሙያዎች ተቋሙ በሚያወጣው የውስጥ ማስታወቂያ ተወዳድረው የኃላፊነት ድርሻ እንደሚኖራቸው፣ ከዚህ ባለፈ ግን በጎደሉ ቦታዎች ደግሞ የውጭ ማስታወቂያ ወጥቶ የአዳዲስ የሥራ ኃላፊዎችና ሙያተኞች ቅጥር የሚፈጸም ስለመሆኑም ተነግሯል፡፡