ሐሙስ ሚያዝያ 11 ቀን 2010 ዓ.ም. ረፋድ ላይ በፓርላማ በነበረ ስብሰባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የካቢኔ አባላት ሹመት አፀድቀዋል፡፡ ተሿሚዎቹም ቃለ መሃላ ፈጽመዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቀረቡ ተሿሚዎች መካከል አሥሩ አዳዲስ ሲሆኑ፣ ስድስቱ ደግሞ ከአንዱ ወደ ሌላው የሚኒስትርነት ኃላፊነት የተዘዋወሩ ናቸው፡፡ ከካቢኔ አባላቱ በተጨማሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ አባዱላ ገመዳ ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ተሰናብተው፣ በምትካቸው ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል ተጠቁመው ለመጪዎቹ ሁለት ዓመታት አፈ ጉባዔነቱን ተረክበዋል፡፡ ቃለ መሃላም ፈጽመዋል፡፡ አቶ አባዱላ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የደኅንነት አማካሪ ተደርገዋል፡፡ በዕለቱ የግብርና እና የእንስሳት ሀብት ሚኒስቴርን እንደ አዲስ ለማደራጀት የቀረበው ረቂቅ አዋጅም በሦስት ተቃውሞና በአንድ ድምፀ ተአቅቦ በአብላጫ ድምፅ ፀድቋል፡፡ ይህ አዋጅ በምክር ቤቱ አባላት ጥያቄዎችና ተቋውሞዎች ቀርበውበት ነበር፡፡ ከፓርላማው ውሎ በኋላ የተለያዩ ሹመቶችም ተሰጥተዋል፡፡