ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በጎንደር ከተማ ተገኝተው ከከተማዋና ከአጎራባች ወረዳዎች ከመጡ ነዋሪዎች ጋር ውይይት አደረጉ፡፡
ዓርብ ሚያዝያ 12 ቀን 2010 ዓ.ም. ከማለዳው የጀመረው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት፣ በመጀመርያ በአፄ ፋሲል ስታዲዮም ለተሰበሰቡ በሺዎች ለሚቆጠሩ የከተማዋና የአጎራባች ወረዳ ነዋሪዎች ንግግር አድርገዋል፡፡ በባህላዊ ጃኖ ልብስ ደምቀው የታዩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው፣ ‹‹ይህ ሕዝብና ይህ ምድር በገዥዎች ጭካኔ በትር ይሳደዱ የነበሩ በርካታ ኢትዮጵያውያንን ሕይወት ለማትረፍ መስዋዕትነት የከፈለ፣ ኢሕዲንን የመሠረቱት ያልተንበረከኩ ቆራጥ ታጋዮች ያፈራ ሕዝብ ነው፤›› ሲሉ አሞካሽተዋል፡፡
‹‹ባሳለፍናቸው ትግሎች በርካታ የአማራ ወጣቶች በአደባባይ ተረሽነው ሬሳቸው ሜዳ ተጥሏል፣ ታስረዋል፣ ተገርፈዋል፣ አካላቸው ጎሏል፤›› ሲሉ ዘክረዋል፡፡ ጎንደር ለማዕከላዊ መንግሥት ምሥረታ ያደረገችውን አስተዋጽኦና ታሪካዊ አበርክቶዋን ዳሰዋል፡፡
በተጨማሪም ሕዝቡ ከጎናቸው እንዲቆምና እንዲያግዛቸው ጠይቀዋል፡፡ ‹‹ከጎናችን እስካላችሁ ድረስ በምንችለው ፍጥነትና መጠን ተረባርበን በመሥራት በጥበብ የማናቋርጠው የሕይወት እክል በፍፁም ሊኖር አይችልም፤›› ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው፣ እንዲሁም ከሌሎች የክልሉ ባለሥልጣናት ታጅበው ከሕዝቡ ጋር ውይይት አድርገዋል፡፡ በውይይታቸውም ከተለያዩ አካላትና ግለሰቦች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በውይይቱ ወቅት ከወልቃይት ጉዳይ ጋር በተያያዘ ለተነሳላቸው ጥያቄ፣ ጉዳዩ በሕግ አግባብ ሊፈታ እንደሚችል፣ ሕገ መንግሥቱም ይህን ጉዳይ ሊፈታ ይችላል ብለው መናገራቸው ተደምጧል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቀጣይ ከወልቃይት ኮሚቴ አባላት ጋር ተገናኝተው በጉዳዩ ላይ እንደሚወያዩ መናገራቸውን፣ የአማራ ብዙኃን መገናኛ ኤጀንሲ ዘገባ ያመለክታል፡፡
ከሁለቱ ዓመት በፊት የወልቃይት ኮሚቴ አባላትን በቁጥጥር ሥር ለማዋል ከፀጥታ ኃይሎች ጋር በተፈጠረ ችግር፣ ጎንደር ከተማን ጨምሮ በክልሉ የሕዝብ ተቃውሞና የፀጥታ ችግር ማጋጠሙ ይታወሳል፡፡
በቁጥጥር ሥር ውለው የነበሩ የወልቃይት ኮሚቴ አባላትም በቅርቡ ከእስር መፈታታቸው ይታወሳል፡፡
በሱዳን ድንበር ላይ ከሚከሰቱ ግጭቶችና ከመሬት ጥያቄ ጋር በተያያዘም ባህር ዳር ለጣና ፎረም ጉባዔ ይመጣሉ ተብሎ ከሚጠበቁት የሱዳን ፕሬዚዳንት ኦማር ሐሰን አል በሽር ጋር ውይይት እንደሚያደርጉ፣ ለጊዜው ድንበር ላይ የሠፈሩ የሁለቱም አገሮች ወታደሮች ገለል እንዲሉ ይደረጋሉ ብለዋል፡፡
በተጨማሪም ከመሠረተ ልማት መጓደል ጋር በተያያዘ አዳዲስ መንገዶች፣ ትምህርት ቤቶች፣ በቂና በጥራት እንደሌላቸው ተጠይቀዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩም፣ ‹‹ያነሳችኋቸው የመሠረተ ልማት ግንባታ ጥያቄዎች ማለትም እዚሁ ወረዳን ከወረዳ ጋር ማገናኘት፣ ዞን ከዞን ጋር ማገናኘት የፌዴራል መንግሥትን አይመለከትም፡፡ ይኼ የክልል መንግሥት ኃላፊነት ነው፤›› ብለው የፌዴራል መንግሥት ዋና ሥራ ጎንደርን ወደ ትግራይ ወደ ሱዳን ከዚያም ሲያልፍ በወሎ በኩል ከጂቡቲ ጋር ማገኛነትና ከዚያም ባለፈ በክልል አቅም የማይሠሩ ኢንዱስትሪዎችን መገንባት ነው በማለት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የጎንደር ጉብኝታቸውን ጨርሰው ወደ ባህር ዳር አቅንተዋል፡፡ በባህር ዳር ቆይታቸውም ከከተማዋ ነዋሪዎች ጋር ውይይትና ምክክር እንደሚያደርጉና የጣና ፎረም ስብሰባን እንደሚሳተፉ የተያዘላቸው መርሐ ግብር ያስረዳል፡፡