አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሳይንስና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ አቋቋመ፡፡ በከተማው ለመጀመርያ ጊዜ የተቋቋመው ይህ ኤጀንሲ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ እንዲሁም የፈጠራ ባለሙያዎች የተካተቱበት አማካሪ ምክር ቤት ይኖረዋል ተብሏል፡፡
የሳይንስና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲው ተጠሪነቱ በቀጥታ ለከተማው ከንቲባ ሲሆን፣ ኤጀንሲውን እንዲመሩ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ የነበሩት አቶ ኃይለ ሥላሴ ፍሰሐ ዋና ዳይሬክተር ሆነው ተሾመዋል፡፡ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ መሐመድ አህመዲን የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ሆነው በመሾማቸው፣ የከተማው አስተዳደር በአቶ መሐመድ ቦታ አቶ እንደሻው ጣሰውን የቢሮ ኃላፊ አድርጎ ሾሟል፡፡
አቶ ኃይለ ሥላሴ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በፌዴራል ደረጃ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፖሊሲ ስትራቴጂ ወጥቷል፡፡ ክልሎችና የከተማ አስተዳደር አካላት ከዚሁ ፖሊሲና ስትራቴጂ በመነሳት የራሳቸውን ዕቅድ አውጥተው ተግባራዊ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
‹‹የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርም በዚህ መነሻነት የራሱን ኤጀንሲ አቋቁሞ ወደ ሥራ ገብቷል፤›› በማለት አቶ ኃይለ ሥላሴ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ኤጀንሲውን ማቋቋም ያስፈለገበት ምክንያት በማቋቋሚያ አዋጁ ላይ እንደተጠቀሰው፣ የአዲስ አበባ ከተማ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፍላጎትን ከፌዴራል መንግሥት ሳይንስና ቴክኖሎጂ ፖሊሲና ስትራቴጂ ጋር ለማጣጣም ነው፡፡
ውጤታማ የሆኑ የውጭ ቴክኖሎጂዎችን መምረጥ፣ ማላመድ፣ መጠቀም፣ ማሻሻልና ማስወገድ፣ እንዲሁም አቅም መፍጠርና መቆጣጠር የሚያስችል ኤጀንሲ ማቋቋም አስፈልጓል ተብሏል፡፡
የከተማውን ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ ተግባርና ኃላፊነት ላይ የሚያማክርና አመራር የሚሰጥ አማካሪ ምክር ቤት ተቋቁሟል፡፡
የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ከንቲባው ነው፡፡ ከምክር ቤት አባላት፣ ከትምህርት ተቋማት፣ ከኢንዱስትሪ ዘርፍ፣ ከምርምር ማዕከላት፣ ከጤና ተቋማት፣ እንዲሁም ከግሉ ዘርፍና በሳይንስና ቴክኖሎጂ ፈጠራ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦች አባል ይሆናሉ ተብሏል፡፡