በአዲስ አበባና በወልቂጤ ከተሞች በህቡዕ በመደራጀት፣ በተከሰሱበት የሽብር ወንጀል ድርጊት ከሰባት እስከ 22 ዓመታት በሚደርስ ጽኑ እስራት የተወሰነባቸውን ‹‹የሙስሊሙ ማኅበረሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ›› በሚባል መጠሪያ የሚታወቁትን ፍርደኞች፣ በኃይል ለማስለቀቅ ሲንቀሳቀሱ ተገኝተዋል ተብለው የተከሰሱ 16 ግለሰቦች ታኅሳስ 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ጥፋተኛ ተባሉ፡፡
በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 14ኛ ወንጀል ችሎት ጥፋተኛ የተባሉት ተከሳሾች በእነ ኤልያስ ከድር የክስ መዝገብ የሚጠሩ ናቸው፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ በህቡዕ ተደራጅተው በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ ከሚኖሩ አጋሮቻቸው ጋር በመሆን በህቡዕ እየተገናኙ፣ ጉዳያቸው በሕግ ተይዞ በፍርድ ቤት በመታየት ላይ የነበሩትን እነ አቡበከር አህመድን (18 ሰዎች) በኃይል ለማስለቀቅ፣ የተለያዩ ድርጊቶችን መፈጸማቸውን ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በክሱ አካቷል፡፡
የተለያዩ አባላትን በመመልመልና ‹‹ድምፃችን ይሰማ፣ የሙስሊሙ ማኅበረሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴን በኃይል እናስፈታለን›› የሚል ጽሑፍ የያዙ በራሪ ወረቀቶችን በማዘጋጀት፣ በየመስጊዱ መበተናቸውም በክሱ ተገልጿል፡፡
በተለይ ሙስሊሙ ማኅበረሰብ ተሰባስቦ በሚያከብራቸው በዓላት ላይ አመፅና የቅስቀሳ ጥሪ ወረቀቶችን መበተናቸውንና በየክልሉ በህቡዕ ከተደራጁ ቡድኖች ጋር ግንኙነት ፈጥረው ሲንቀሳቀሱ እንደነበርም በክሱ ተመልክቷል፡፡
‹‹የሙስሊሙ ማኅበረሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ ቢታሰርም እኛ ተክተን እንሠራለን፤›› በማለት የተለያዩ ቅስቀሳዎችን ማድረጋቸውን ዓቃቤ ሕግ በክሱ ጠቅሶ፣ እንደ ክሱ ያስረዱልኛል ያላቸውን ከ50 በላይ ምስክሮች አቅርቦ አሰምቷል፡፡
ተከሳሾቹም እንዲከላከሉ በተሰጠው ውሳኔ መሠረት መከላከያ ምስክሮቻቸውን አሰምተዋል፡፡ የግራ ቀኙን ክርክር የሰማውና የቀረበለትን የሰነድ ማስረጃ የመረመረው ፍርድ ቤቱ ዓቃቤ ሕግ እንደ ክሱ ማስረዳቱን ገልጾ፣ ተከሳሾቹን ጥፋተኛ ብሏቸዋል፡፡ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠትም ለጥር 2 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጥሯቸዋል፡፡