የራሳቸው ሕንፃ የሌላቸውን የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች፣ ከኪራይ የሚገላግል ፕሮጀክት ተቀረፀ፡፡ በእዚህ ፕሮጀክት በአዲስ አበባ ከተማ በሰባት ክላስተሮች 40 ሕንፃዎች እንደሚገነቡ ታውቋል፡፡
የፌዴራል የመንግሥት ቢሮዎች ግንባታ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ኃይለ መስቀል ተፈራ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የሕንፃዎቹ ግንባታ መንግሥት ለኪራይ የሚያወጣውን ወጪ ከማስቀረቱ ባሻገር አገልግሎት አሰጣጡን የተቀላጠፈ ለማድረግ፣ በክላስተር መከፋፈል አስፈልጓል፡፡
እነዚህ ሕንፃዎች አንድ ላይ በሚገነቡበት ወቅት ከሥራ ሰዓት በኋላ ጭር ያለ አካባቢ እንዳይፈጠር የተለያዩ መዝናኛ ማዕከላት አብሮ ለመገንባት መታሰቡንም አቶ ኃይለ መስቀል አመልክተዋል፡፡
የመንግሥት ቢሮዎች ግንባታ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ባካሄደው ጥናት 43 የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የራሳቸው ቢሮ የላቸውም፡፡ በዚህ ዓመትም 15 አዳዲስ መሥሪያ ቤቶች ተቋቁመዋል፡፡
ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ ከገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስቴር መረጃ አሰባስቦ ባካሄደው ጥናት፣ መንግሥት ለቢሮ ኪራይ በዓመት 250 ሚሊዮን ብር ወጪ ያደርጋል፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ በዚህ ዓመት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ 40 ሕንፃዎችን ለመገንባት ዕቅድ አውጥቷል፡፡ ፕሮጀክቱ እውን የሚሆነው በሰባት ቦታዎች ላይ መሆኑም ታውቋል፡፡
ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ጥያቄ የቀረበ ሲሆን፣ አስተዳደሩ የመሬት ጥያቄውን መቀበሉን መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ለቦታ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት አስተዳደሩ በሥሩ ለሚገኘው ለከተማ ማደስና መሬት ባንክ ኤጀንሲ መምራቱ ታውቋል፡፡
የኤጀንሲው ባለሙያዎች በተለይ መልሶ ማልማት ፕሮጀክቶች በሚካሄዱባቸው አካባቢዎች የተጠየቀውን ቦታ ለማቅረብ የመሬት መረጣ እያካሄዱ መሆኑን የአስተዳደሩ ምንጮች ገልጸዋል፡፡
የክላስተር ድልደላው ገና አለመጀመሩን አቶ ኃይለ መስቀል ገልጸው፣ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች እጅብ ብለው ከተገነቡ በኋላ ምሽት ላይ ጭር ያለ ዞን እንዳይፈጠር፣ የተለያዩ የመዝናኛና አገልግሎት መስጫ ተቋማት በተሰባጠረ መልኩ እንደሚገነቡም አመልክተዋል፡፡
መንግሥት ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤቱ ያቀረበውን ዕቅድ ካፀደቀ፣ በፍጥነት ወደ ግንባታ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡