የኢትዮጵያ፣ የግብፅና የሱዳን የውጭ ጉዳይና የውኃ ሚኒስትሮች ከሳምንት በፊት በሱዳን ባደረጉት ስብሰባ ውሳኔ መሠረት፣ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሥር ውኃ መልቀቂያ ቱቦዎች ብዛት ላይ የሦስቱ አገሮች የቴክኒክ ቡድን በአዲስ አበባ ያደረገው ውይይት ያለስምምነት መጠናቀቁ ተሰማ፡፡
ግብፅ በሱዳኑ ስብሰባ ካነሳቸው ሐሳብ አንደኛው የግድቡ የሥር ውኃ መልቀቂያ መስመሮች ከሁለት ወደ አራት ከፍ እንዲሉ ጠይቃ ነበር፡፡
በወቅቱ የግብፅ ጥያቄ ተቀባይነት ያላገኘ ቢሆንም፣ መተማመን ለመፍጠር በጉዳዩ ላይ የቴክኒክ ቡድን ተቋቁሞ ውይይት እንዲደረግ በመስማማት ሚኒስትሮቹ ውሳኔ አሳልፈው ነበር፡፡
በዚሁ ስምምነት መሠረትም አዲስ የተቋቋመው የሦስቱ አገሮች የቴክኒክ ቡድን ባለፈው ታኅሳስ 27 እና 28 ቀን 2008 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ውይይቱን ማድረጉን የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ብዙነህ ቶልቻ ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡
በዚሁ የቴክኒክ ውይይት ላይ የህዳሴው ግድብ ዲዛይን ቀርቦ ውይይት የተካሄደበት መሆኑን የገለጹት አቶ ብዙነህ፣ በኢትዮጵያ በኩል ኃይል አመንጭቶ ከሚፈሰው ውኃ በተጨማሪ ከኃይል ማመንጨት ጋር ግንኙነት የሌለው ሁለት የሥር ውኃ መልቀቂያ በቂ ስለመሆኑ ገለጻ መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ግብፅን ወክሎ የተገኘው ቡድን ደግሞ የሥር ውኃ መልቀቂያ መስመር አራት እንዲሆን መከራከሪያ አቅርቧል፡፡ ሱዳን የኢትዮጵያን አቋም መደገፏም ታውቋል፡፡
በዚህም መሠረት በጉዳዩ ላይ የተወያየው የቴክኒክ ቡድን የውይይቱ ቃለ ጉባዔ ላይ በመፈራረም ለሚኒስትሮች ስብሰባ እንደሚያቀርብ አቶ ብዙነህ አስታውቀው፣ ይህ ስብሰባ መቼ እንደሚሆን በጋራ ቴክኒክ ኮሚቴው ወደፊት የሚወሰን መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የሦስቱ አገሮች መሪዎች የህዳሴውን ግድብ በተመለከተ በተፈራረሙት የመርህ መገለጫ ላይ ብዥታ የፈጠሩ ጉዳዮች በውይይት እንደሚፈቱ፣ ውይይቱም በሙሉ ስምምነት እንደሚወሰን ይገልጻል፡፡
ይኸው የመርህ መገለጫ ስምምነት በጋራ ቴክኒክ ቡድኑ ስምምነት ያልተደረሰበት ጉዳይ ወደ ሚኒስትሮች፣ በሚኒስትሮች ያልተፈታ ከሆነ ወደ መሪዎች እንደሚሄድ ይገልጻል፡፡