‹‹ዓለም አቀፍ ሽብርተኝነት አሁንም በጭካኔና በኢሰብዓዊነት የተሞላውን ገጽታ እያሳየ ነው››
የጀርመን መራሒተ መንግሥት አንገላ መርከል ማክሰኞ ጥር 3 ቀን 2008 ዓ.ም፣ በቱርክ የፋይናንስና የቢዝነስ ከተማ ኢስታንቡል ከደረሰው የቦምብ ፍንዳታ በኋላ ካደረጉት ንግግር የተወሰደ፡፡ በኢስታንቡል በአንድ ሶሪያዊ አጥፍቶ ጠፊ ሳይፈጸም አልቀረም በተባለ የቦምብ ጥቃት አሥር ሰዎች ተገድለው 15 ሲቆስሉ፣ ከሟቾችና ከቆሰሉት መካከል አብዛኞቹ ጀርመናውያን ቱሪስቶች ናቸው፡፡ አንገላ መርከል፣ ‹‹ዛሬ ኢስታንቡል፣ ከዚያ በፊት ፓሪስ፣ ቱኒዝያና አንካራ ጥቃቶች ተፈጽመውባቸዋል፤›› ብለው፣ ድርጊቱን ጭካኔና ኢሰብዓዊነት ሲሉ ገልጸውታል፡፡ በኢስታንቡል በብዛት ቱሪስቶች በሚያዘወትሩበት ሥፍራ የተፈጸመው የቦምብ ጥቃት ፍንዳታው ከፍተኛ እንደነበር፣ አፈንድቷል የተባለው የ28 ዓመቱ ሶሪያዊ ተጠርጣሪ ከእነማን ጋር ግንኙነት እንዳለው እየተጣራ መሆኑን የቱርክ ባለሥልጣናት መናገራቸው ተሰምቷል፡፡ በምሥሉ ላይ የሚታየው የቦምብ ጥቃቱ የተፈጸመበት ሥፍራ በፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ሥር ከዋለ በኋላ ነው፡፡