ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሔደው ‹‹ኢንተርናሽናል ቢውቲ ኤንድ ኮስሞቲክስ ኤክስፖ›› ከተነሳበት ዓላማዎች አንዱ ተፈጥሯዊ ንጥረ ነገሮችን በመጠቀም መዋቢያ የሚያዘጋጁ የሀገር ውስጥ ባለሙያዎችን ማስተዋወቅ ነው፡፡ በሀገራችን ኸርብ (የተፈጥሮ ቅጠል) በመጠቀም የተለያዩ መዋቢያዎች ቢዘጋጁም ተጠቃሚዎቹ ውስን እንደሆኑ ይነገራል፡፡ ሀገር ውስጥ ከሚሠሩ መዋቢያዎች በበለጠ ውጪ የሚዘጋጁት የተሻለ ዕውቅናና ገበያ እንዳላቸውም ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
ይህን ሀሳብ ከሚጋሩት አንዱ የኤክስፖው አዘጋጅ ግሬአትሮ ፕሮሞሽን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ መርጀን አህመድ ሲሆን፣ ሀገርኛ መዋቢያዎችን የሚያዘጋጁ ግለሰቦች አልያም ድርጅቶች ከተጠቃሚው ጋር በስፋት እንዳልተገናኙ ይገልጻል፡፡ እንደምክንያት የሚጠቅሰውም የመረጃ ክፍተት መኖሩንና የአምራቶቹ አቀራረብ ገበያ ተኮር አለመሆኑን ነው፡፡
ምርቶቻቸውን ለገበያ ሲያቀርቡ ትኩረት ሳቢ ካለመሆናቸው ባሻገር፣ ጠንካራ የንግድ ሰንሰለት ተፈጥሯል ብሎ አያምንም፡፡ ይህንን ለመለወጥም በተለያዩ ጊዜአት የምርት አቀራረብና አሻሻጥ ሥልጠና የሰጡ ሲሆን፣ ኤክስፖው ደግሞ የአምራቾቹን ተደራሽነት እንደሚያሰፋው ያምናል፡፡
በኤክስፖው ምርቶቻቸውን ባይሸጡ እንኳን ከገዥዎች እንዲሁም ከተለያዩ ተቋሞች ጋር ትስስር እንደሚፈጥሩም ይናገራል፡፡ ‹‹ምርቶቹን የሚሠሩት ባለሙያዎች መዋቢያዎቹ ምን ጥቅም እንዳላቸው ለሰዎች ያስረዳሉ፤ ይህም ታዋቂነታቸውን ያሰፋዋል፤›› ይላል፡፡ ኤክስፖው ከሀገር ውስጥ አምራቾች በተጨማሪ እንደ ኒቪያና አክስ ያሉ ወደ አሥር የሚጠጉ ዓለም አቀፍ አምራቾችንም ያሳተፈ ነው፡፡
ጥር 4 ቀን 2008 ዓ.ም. በኤግዚቢሽን ማዕከል የተከፈተውና እስከ ጥር 8 ቀን 2008 ዓ.ም. በሚቆየው ኤክስፖው፣ ልዩ ልዩ መዋቢያዎች ለዕይታና ለሽያጭም ቀርበዋል፡፡ እንደ አቶ መርጀን ገለጻ፣ ብዙ ሰዎች ውበትና ኮስሞቲክስን ከቅንጦት ጋር ሲያያዙ ይስተዋላል፡፡ ‹‹በርካታ ተጠቃሚዎች የውበት ጉዳይ ከጤናና ራስን ከመጠበቅ ጋር ትስስር እንዳለው አያስተውሉም፤ ሰው ስለሚጠቀምበት ምርት አውቆ ሳይሆን በልምድ እንዲሁ ይሸምታል፤›› ይላል፡፡
ይህን ልማዳዊ አካሔድ ለማስተካከል እንዲቻልና ስለ መዋቢያዎች ተጨባጭ መረጃ የሚሰጡ መሰል ኤክስፖዎች አስፈላጊ እንደሆኑ ይገልጻል፡፡ ኤክስፖው ለተጠቃሚዎች በመዋቢያ ረገድ ያሉትን አማራጮች እንደሚያመላክትም አክሏል፡፡ ስለ መዋቢያዎችና ተያያዥ ጉዳዮች መረጃ እንዲሰጡ የጤና ባለሙያዎች፣ የሥነ ልቦና ባለሙያዎች፣ ስፖዎች፣ ሆቴሎችና ሌሎችም ጉዳዩ የሚመለከታቸው ተቋሞች ተጋብዘዋል፡፡
በኤክስፖው ከቀረቡ መዋቢያዎች በተጨማሪ፣ በፋሽንና የውበት ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች የተዘጋጁ የፋሽን ትዕይንቶችም ቀርበዋል፡፡ ተማሪዎቹ ሥራዎቻቸውን እንዲያሳዩና ዕውቅና እንዲያገኙ ያለመ እንደሆነም አዘጋጁ ተናግሯል፡፡
ኤክስፖው ዘንድሮና በሚቀጥለው ዓመት፣ በዓመት አንድ ጊዜ እንዲዘጋጅና ከዚያ በኋላም በዓመት ሁለት ጊዜ የማዘጋጀት ዕቅድ እንዳላቸው አክሏል፡፡