የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የነበሩት አቶ ጌታቸው አምባዬ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የሕግ አማካሪ ሆነው ተሾሙ፡፡
በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አዲሱ ካቢኔ ባለመካተታቸው ርዕሰ ጉዳይ ሆነው የቆዩት አቶ ጌታቸው፣ ከግንቦት 10 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕግ አማካሪ ሆነው መሾማቸውን ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡
በ1982 ዓ.ም. ኢሕዴን/ብአዴንን የተቀላቀሉት አቶ ጌታቸው፣ በአማራ ክልል ከወረዳ እስከ ክልል በተለያዩ የሥልጣን ዕርከኖች ሠርተዋል፡፡
በአማራ ክልል የክልል ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባዔ፣ የማስታወቂያ ቢሮ ኃላፊና የብአዴን የፕሮፓጋንዳ ክፍል ኃላፊ ሆነው የሠሩባቸው ይገኙባቸዋል፡፡
በኋላም ወደ አዲስ አበባ ከተማ በመምጣት የአዲስ አበባ ኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሆነው የሠሩ ሲሆን፣ በኋላም በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማው መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ኃላፊ ነበሩ፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ ከዋናዎቹ ክፍሎች ተርታ በሚመደበው በመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ መደብ ላይ ብዙም ሳይቆዩ፣ በ2005 ዓ.ም. ወደ ፌዴራል መንግሥት በመዛወር የፍትሕ ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል፡፡
ፍትሕ ሚኒስትርን ወደ ፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በማሸጋገር ሒደት ዋነኛ ተዋናይ የነበሩት አቶ ጌታቸው፣ በኢሕአዴግ ዘመነ መንግሥት የመጀመርያው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ሆነው ተሹመው እስካለፈው ወር ድረስ በኃላፊነት ቆይተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር አዲስ ካቢኔ ሲያቋቁሙ ያልተካተቱት አቶ ጌታቸው፣ አንድ ደረጃ ዝቅ ብለው በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ አማካሪ ሆነው ተሹመዋል፡፡
አቶ ጌታቸው ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ በሕግ የመጀመርያ ዲግሪ፣ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ደግሞ ከአሱዛ ፓስፊክ ዩኒቨርሲቲ በኦርጋናይዜሽናል ሊደርሺፕ የትምህርት ዘርፍ አግኝተዋል፡፡