የስሜን ተራራዎች ማህበረሰብ አቀፍ ቱሪዝም ግብረ ሰናይ ማኅበር በኢትዮጵያ ኗሪዎች በጎ አድራጎት ማኅበርነት በምዝገባ ቁጥር 3448 የስሜን ተራራዎች ማህበረሰብ አቀፍ ቱሪዝም ድርጅት ሆኖ ለማገልገል በ2007 ዓ.ም. የተቋቋመ ድርጅት ነው፡፡
ማኅበሩ የአካባቢው ማኅበረሰብ የባህል የቱሪዝምና የመንደር ጉብኝት በማከናወን ገቢ በማግኘት የኑሮ ደረጃውን እንዲያሻሽል ማገዝን ዓላማው ያደረገ ሲሆን፤ በዚህ የባህልና የመንደር ጉብኝት እንቅስቃሴ ላይ የማኅበረሰቡ የምግብ አዘገጃጀት፤ የእንጀራና ወጥ አሠራር፣ ቡና አፈላል፣ የኮረፌ አጠማመቅ፣ የፀጉር አሠራርና ሌሎች ነገሮችን የሚያካትት ነው፡፡ በዚህ ተግባር የተሰማሩት የብሔራዊ ፓርኩ ዙሪያ ነዋሪዎች በማስጎብኘትም የእንቅስቃሴው ዋና ተዋናይ በመሆን ገቢ የሚያገኙ ይሆናል፡፡ በዚያም ኑሯቸውን ይደጉማሉ ተብሎ ይታመናል፡፡ ይህ ሲሆን ታዲያ የብሔራዊ ፓርኩ መጠበቅ ተስፋ ሰጭ ሆኖ ይቀጥላል፤ ለዚህም ማኅበረሰቡ እንደራሱ ሀብት በመመልከት ብሔራዊ ፓርኩን ከአደጋ መዝገብ ለማውጣት ለሚደረገው እንቅስቃሴ አጋዥ በመሆን እንደሚሠራ ይጠበቃል፡፡
የማኅበረሰብ አቀፍ ቱሪዝም ግብረ ሰናይ ማኅበር ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ድጋፍ ሲደረግለት ቆይቷል፡፡ ኤጀንሲው እስከ 2008 ዓ.ም. ታኅሣሥ ወር ድረስ ለአራት ተከታታይ ዓመታት በስሜን ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፣ ድጋፍ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን፣ ከዚህ በኋላም ሙሉ ሥራውን ለተቋቋመው ግብረ ሰናይ ድርጅት የሚያስረክብ ይሆናል፡፡
ለማኅበሩ የመጀመሪያ የሆነው የገቢ ማሰባሰቢያ ኮንሰርትም ይካሄዳል፡፡ ኮንሰርቱ በኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ባለሥልጣን (ኢዱልጥባ)፣ በጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ)፣ የሰሜን ተራሮች ማኅበረሰብ አቀፍ ቱሪዝም ግብረ ሰናይ ማኅበርና ቻቺ ኢንተርናሽናል አርት ማኔጅመንት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የኢዱልጥባ የበጎ ፈቃድ አምባሳደር አርቲስት ቻቺ ታደሰ አማካይነት ጥር 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ የሚከናወን ይሆናል፡፡
ኮንሰርቱ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችንና ባለሀብቶችን ለድጋፍ የሚያሳትፍ ሲሆን በሥነ ሥርዓቱ ላይ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የተለያዩ አገሮች አምባሳደሮች፣ ባለሀብቶችና ሌሎች ግለሰቦች እንደሚገኙ ይጠበቃል፡፡ በዝግጅቱ ፊልሞች፣ ተፈጥሮን ማዕከል ያደረጉ የጨረታ ፕሮግራሞችም ይኖራሉ፡፡ የመንደር ጉብኝት እንቅስቃሴዎችን የሚያሳይ ፊልምም በመድረኩ ለእይታ ይቀርባል፡፡
ለስሜን ተራራዎች ማኅበረሰብ አቀፍ ቱሪዝም የገቢ ማሰባሰቢያ ኮንሰርት ጥር 15 ቀን 2008 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ የሚከናወን ይሆናል