Friday, June 9, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

ክቡር ሚኒስትር

[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ ቢሯቸው ገባች]

  • ምን ፈለግሽ?
  • ከሰዓት አልኖርም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለምን ሲባል?
  • ጥምቀት ነዋ፡፡
  • ጥምቀት ነገ አይደል እንዴ?
  • ዛሬ ከተራ ነዋ፡፡
  • ከተራ ምንድን ነው?
  • ታቦት የሚወጣበት ቀን ነዋ፡፡
  • ስለዚህ ታቦት ሲወጣ፣ አንቺ ከሥራ መውጣት አማረሽ?
  • ክቡር ሚኒስትር ምን ነካዎት?
  • ንገሪኝ አንቺ የመሥሪያ ቤታችን ታቦት ነሽ ወይ?
  • ምን እያሉ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ታቦት ይወጣል ብለሽ አንቺም ከሥራ የምትወጪው?
  • ታቦቱን እሸኘዋለኋ፡፡
  • ሞክሪውና እኔም ከሥራ እሸኝሻለሁ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር በዚህማ ቀልድ የለም፡፡
  • እንዴት?
  • እርስዎ በአብዮታዊ ዴሞክራሲ እንደማይቀልዱ እኔም በሃይማኖቴ አልቀልድማ፡፡
  • እና ሥራ ጥለሽ ነው የምትሄጂው?
  • እርስዎ ሥራ ጥለው ስብሰባ ይሄዳሉ አይደል እንዴ?
  • ስብሰባ ሥራ አይደለም ያለሽ ማን ነው?
  • ሕዝቡ ነዋ፡፡
  • እንዴት?
  • ተሰብስበው መፍትሔ ካላመጡ፣ ስብሰባ በራሱ ማድረጉ መፍትሔ አያመጣማ፡፡
  • ለማንኛውም ያልተጠየቅሽውን አታውሪ፡፡

[አንድ የባንክ ባለሙያ ለክቡር ሚኒስትሩ ደወለላቸው]

  • ምንድን እየተሠራ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ሥራ ነዋ፡፡
  • እኮ ምን ዓይነት ሥራ?
  • ምን እያወራህ ነው?
  • ለምን አንደኛውኑ አትዘጉንም?
  • ማንን ነው የምንዘጋው?
  • የግል ባንኮችን ነዋ፡፡
  • ኢኮኖሚውን ያለ ግል ዘርፉ ማካሄድ እኮ በአንድ እጅ እንደማጨብጨብ ነው፡፡
  • ከዚህ በላይ እንዴት በአንድ እጅ ታጨበጭቡ ታዲያ?
  • አልገባኝም?
  • ይኸው በንግድ ባንክ ብቻ ማጨብጨብ ከጀመራችሁ እኮ ሰነባበታችሁ፡፡
  • ቅኔ እያወራህ ነው?
  • ምን ቅኔ ነው እውነታ ነው እንጂ፡፡
  • የምን እውነታ?
  • ሰሞኑን ከግል ባንኮች የወጣው ገንዘብ ምን ያህል እንደሆነ አልሰሙም?
  • ኧረ አልሰማሁም፡፡
  • ወደ 4.5 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገንዘብ በሁለት ሳምንታት ከግል ባንኮች ወጥቷል፡፡
  • ሰው ብሩን በካዝና ማስቀመጥ ጀመረ እንዴ?
  • የለም ንግድ ባንክ የሚሉት ካዝና ውስጥ ከቶት ነው እንጂ፡፡
  • ምነው ዛሬ አሽሙር አበዛህ?
  • ወድጄ አይደለም፣ አካሄዳችሁ ስላልገባኝ ነው፡፡
  • የምን አካሄድ?
  • ክቡር ሚኒስትር ይህ ገንዘብ በአንዴ ከግል ባንኮች ለምን እንደወጣ ያውቃሉ?
  • አላውቅም፡፡
  • ንግድ ባንክ ኤልሲ ለሚፈልግ ደንበኛ ሁሉ እሰጣለሁ በማለቱ ነዋ፡፡
  • እኔ እኮ የማይገባኝ አንድ ነገር ነው፡፡
  • ምንድን ነው የማይገባዎት?
  • በየሚዲያው ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት አለ እየተባለ ሲወራ ታግሰን ዝም አልን፡፡
  • እውነት ነዋ፡፡
  • አሁን ደግሞ ኤልሲ ለከፈተ እንሰጣለን ሲባል ደግሞ አገር ተተራመሰ ትላላችሁ፡፡
  • በእርግጥ ተተራምሷላ፡፡
  • ምን ተሻለ ታዲያ?
  • በተጠና አካሄድ ውሳኔዎችን ማከናወን ነዋ፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ክቡር ሚኒስትር የፋይናንስ ዘርፉ ጥንቃቄ የተሞላበት አካሄድ ይጠይቃል፡፡
  • እሱማ ልክ ነው፡፡
  • እናንተ ግን እሱን እያደረጋችሁ አይደለም፡፡
  • እንዴት አይደለም?
  • የውድድሩ ሜዳ ፍትሐዊ አይደለም፡፡
  • ለምንድን ነው ፍትሐዊ ያልሆነው?
  • ሁሉም ነገር በንግድ ባንክ በኩል ነዋ የሚፈጸመው፡፡
  • ሁሉም ነገር ስትል?
  • ዶላር ቢመጣ የሚሰጠው ለእሱ ነው፡፡
  • እ…
  • ኮንዶሚኒየም ቤት ሲሠራ በእሱ በኩል ነው፡፡
  • ሌላስ?
  • እኛ ቦንድ እንገዛለን፣ እሱ አይገዛም፡፡
  • እ…
  • ብቻውን ጡንቻውን እያፈረጠማችሁት ነው፡፡
  • እሱ ልጃችን ነዋ፡፡
  • እኛ የእንጀራ ልጆች ነን?

[አንድ ባለሀብት ክቡር ሚኒስትሩ ጋ ደወለ]

  • እንኳን አደረሰዎት ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለምኑ?
  • ለጥምቀት በዓል ነዋ፡፡
  • እኔ እኮ እንዲህ ዓይነት በዓል ብዙም አላከብርም፡፡
  • ለምን እንደማያከብሩት ገባኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ለምንድን ነው የማላከብረው?
  • ለእርስዎ ሁሌ ጥምቀት ነዋ፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • የጥምቀት በዓል መገለጫው እኮ መወራወሩ ነው፡፡
  • ድንጋይ ውርወራ አለበት እንዴ?
  • የለም የለም፣ ሎሚ መወራወሩን ነው የምልዎት፡፡
  • ሎሚ ለምንድን ነው የሚወረወረው?
  • ወንዱ ሴቷን ወድጄሻለሁ ለማለት ሎሚ ይወረውራል፡፡
  • ሴቷስ ምን ትወረውራለች?
  • ሴቷማ ከወደደችው ልቧን ትወረውራለች፡፡
  • እና ይኼ ባህል አሁንም አለ?
  • ባህሉ እንኳን አለ የሚወረወረው ነገር ግን ጨምሯል፡፡
  • ሎሚ መወርወር ቀርቶ ብርቱኳን ተጀመረ?
  • ክቡር ሚኒስትር ምን ነካዎት?
  • እንዴት?
  • በዕድገቱ ሳቢያ ሎሚ ወደ ቪትስ ተቀይሯል፡፡
  • እሱስ ልክ ብለሃል፤ አገሪቷ እኮ ተመንድጋለች፡፡
  • ለማንኛውም እንኳን አደረስዎት፡፡
  • በነገራችን ላይ አንድ ነገር ከንክኖኛል፡፡
  • ምን ከነከንዎት ክቡር ሚኒስትር?
  • ለእርስዎ ሁሌ ጥምቀት ነው ያልከኝ ነዋ፡፡
  • አይ እርስዎ ሁሌም ይወራወራሉ ብዬ ነዋ፡፡
  • ከማን ጋር ነው የምወራወረው?
  • ከባለሀብቶች ጋር ነዋ፡፡
  • ምንድን ነው የምወራወረው?
  • እነሱ ቪላ ሲወረውሩልዎት፡፡
  • እ…
  • እርስዎ ደግሞ መሬት ይወረውራሉ፡፡
  • ኧረ ሰው እንዳይሰማህ?
  • ችግሩ ሰው መስማቱ አይደለም፡፡
  • ታዲያ ምንድን ነው ችግሩ?
  • የሚሰማው ሰው ራሱ ይወራወራል ወይስ አይወራወርም? የሚለው ነው ጥያቄው፡፡
  • ለማንኛውም ምን ፈልገህ ነው?
  • ልጠይቅዎት ነዋ፡፡
  • ምንድን ነው የምትጠይቀኝ?
  • ምን ልወርውርልዎት?
  • ቪትስ እንደማልልህ ታውቃለህ?
  • እሷንማ ብወረውርልዎት መቼ ይቀልቧታል?
  • እንዴት?
  • ሽል ነዋ የሚሉኝ፡፡
  • ለነገሩስ እውነትህን ነው፡፡
  • ስለዚህ ምን ልወርውር?
  • ቪላ ወይ ቪ-8 ነዋ፡፡
  • እርስዎስ ምን ይወረውሩልኛል?
  • ምን ልወርውርልህ?
  • መሬት!

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሹፌራቸው ጋር እየሄዱ ነው]

  • ክቡር ሚኒስትር ያው ነገ አልኖርም፡፡
  • ለምን ሲባል?
  • ጥምቀት ነዋ፡፡
  • ቢሆንስ ታዲያ?
  • ክቡር ሚኒስትር ትልቅ በዓል እኮ ነው፡፡
  • ትልቅ በዓል?
  • አዎ፣ ይኸው ዩኔስኮ ራሱ ሊመዘግበው እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡
  • አሁን አንድ ኒዮሊብራል ተቋም መመዝገቡ ነው ትልቅ የሚያስብለው?
  • ክቡር ሚኒስትር ፖለቲካ ብዙም አይገባኝም፡፡
  • በዓሉ መመዝገብ ካለበት ለምን ልማታዊ በሆኑ የአገራችን ተቋማት አይመዘገብም?
  • አልገባኝም፣ የት መመዝገብ ይችላል?
  • ለምሳሌ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ጽሕፈት ቤት፡፡
  • እ…
  • እንዲያውም በአገራችን ባሉ ልማታዊ ተቋማት መመዝገቡ የውጭ ምንዛሪ ያድንልናል፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • ለኒዮሊብራሎቹ ተቋማት ለምዝገባ የሚከፈለው ገንዘብ በዶላር ነዋ፡፡
  • ኧረ ዩኔስኮ በገንዘብ አይመስለኝም የሚመዘግበው፡፡
  • እሱን እንኳን ተወው፡፡
  • እንዴት?
  • የአገራችን ኩባንያዎች የጥራት ሠርተፊኬት እያሉ የሚያግበሰብሱትን እየከፈሉ አይደል እንዴ የሚያመጡት?
  • እሱን አላውቅም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ስማ እንዲያውም ይኼ ኒዮሊብራል ተቋም መመዝገብ ያለበት ትልቅ ሕዝባዊ በዓል አለን፡፡
  • የምን ሕዝባዊ በዓል?
  • ብሔር ብሔረሰቦች!

[ክቡር ሚኒስትሩ ሊከፍቱት ላሰቡት የሞባይል ቤት ዲስፕሌይ የሠራላቸው ባለሙያ ደወለ]

  • በሰጡኝ ትዕዛዝ መሠረት ሥራዬን ጨርሻለሁ፡፡
  • ዋጋ ቀንስልኛ?
  • ነጋዴ ዋጋ ይጨምራል እንጂ መቼ ይቀንሳል?
  • ለምን አይቀንስም?
  • ከእናንተ ነዋ የምንማረው?
  • እኛ ምን አስተማርናችሁ?
  • ይኸው የነዳጅ ዋጋ ቀንሶ እናንተ መቼ ትቀንሳላችሁ?
  • እ…
  • እንዲያውም መንግሥት ነዳጅ ላይ እንትን ሆኗል ነው የሚባለው፡፡
  • ምን?
  • ኪራይ ሰብሳቢ!

[ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸውን አስጠሩት]

  • ፈለጉኝ ክቡር ሚኒስትር?
  • ከተማ ውስጥ ጥሩ የሚባለው ሞል ላይ አንድ ሱቅ ፈልግልኝ፡፡
  • የምን ሱቅ?
  • የሞባይል መሸጫ የሚሆን፡፡
  • ለማን ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ለእኔ ነዋ፡፡
  • እ…
  • አገሪቷ ስታድግ የበይ ተመልካች መሆን የለብንም፡፡
  • እና?
  • በቃ አሪፍ ሱቅ መክፈት አለብኝ፡፡
  • ኪራዩን ማን ይከፍለዋል፡፡
  • መሥሪያ ቤቱ ነዋ፡፡
  • እንደዛ ከሆነማ ስምዎት ይቀየራል፡፡
  • እንዴት?
  • ክቡር ሚኒስትር ቀርቶ …
  • ማን ልባል?
  • ክቡር ነጋዴ! 

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

አገር የሚገቡ የግል ዕቃዎችን በሚገድበው መመርያ ምክንያት በርካታ ንብረቶች በጉምሩክ መያዛቸው ተገለጸ

በአየር መንገድ ተጓዦች ወደ አገር የሚገቡትን የግል መገልገያ ዕቃዎች...

አዋሽ ባንክ ለሁሉም ኅብረተሰብ የብድር አገልግሎት የሚያስገኙ ሁለት ክሬዲት ካርዶች ይፋ አደረገ

አዋሽ ባንክ ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች በዘመናዊ መንገድ ብድር ማስገኘት...

ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚጓዙ በርካታ ሰዎች ወደ ከተማዋ እንዳይገቡ በፖሊስ መከልከላቸውን ገለጹ

‹‹የኦሮሚያ ክልል መፍትሔ እንዲሰጥበት አሳውቀናል›› የአማራ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ‹‹ጉዳዩ...

ሒጂራ ባንክ የ143 ሚሊዮን ብር ኪሳራ አስመዘገበ

በኢትዮጵያ ሙሉ ለሙሉ ከወለድ ነፃ ባንክ አገልግሎት ለመስጠት ወደ...
- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

ወልቃይትን ማዕከል ያደረገው የምዕራባዊያን ጫና

በትግራይ ክልል የተከሰተው የዕርዳታ እህል ዘረፋ የዓለም አቀፍ ተቋማት...

ከቀጣዩ ዓመት በጀት ውስጥ 281 ቢሊዮን ብሩ የበጀት ጉደለት ነው ተባለ

ለቀጣዩ በጀት ዓመት ከቀረበው 801.65 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ በጀት...

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው አሠራር ወጣ ያለውን ‹‹የወደፊት ግብይት›› ሥርዓት በይፋ አስጀመረ

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው የማገበያየት ተግባሩ ወጣ ያለና በኢትዮጵያ...

የባንክ ማቋቋሚያ መሥፈርት እንደሚጠነክር ሚኒስትሩ ተናገሩ

 ባንኮች ስለውህደት እንዲያስቡም መክረዋል በኢትዮጵያ ውስጥ ባንክ ለማቋቋም የሚያስፈልገው መሥፈርት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ አመሻሹን መኖሪያ ቤታቸው ሲደርሱ ባለቤታቸው በቴሌቪዥን የሚተላለፈው የማዕከላዊ ኮሚቴ ገለጻ እየተከታተሉ አገኟቸውና አጠገባቸው ተቀምጠው የደረሱበትን አብረው መከታተል እንደጀመሩ፣ ባለቤታቸው ቴሌቪዥኑን ትተው መጠየቅ...

እኔ ምለው? እሺ... አንቺ የምትይው? የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ አባላት እንዲያወሩ ወይም እንዲጠይቁ አይፈቀድም እንዴ? እንዴት ይከለከላል? ታዲያ ለምንድነው ፕሬዚዳንቱ ብቻ የሚያወሩት? እያወሩ አይደለም፣ ገለጻ እያደረጉ ነው። ቢሆንም አንድም አባል...

[ክቡር ሚኒስትሩ አምሽተው ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው ‹‹ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ሕዝባችንን እናሻግራለን›› የሚለውን የቴሌቪዥን ዜና ተመልክተው ለብቻቸው ሲስቁ አገኟቸው]

ስልክ እያወራሽ ነበር እንዴ? ኧረ በጭራሽ... ምነው? ታዲያ ምንድነው ብቻሽን የሚያስቅሽ? አይ... በቴሌቪዥኑ የሚቀርበው ነገር ነዋ። ምንድነው? ድሮ ድሮ ዜና ለመስማት ነበር ቴሌቪዥን የምንከፍተው፡፡ አሁንስ? አሁንማ ቀልዱን ተያይዘውታል... አንተ ግን በደህናህ...

[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ስልካቸው ጠራ። ደዋዩ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ኃላፊ እንደሆኑ ሲነገራቸው የስልኩን መነጋገሪያ ተቀበሉ]

ሃሎ፡፡ እንዴት አሉ ክቡር ሚኒስትር። ደህና ነኝ። አንተስ? አስተዳደሩስ? ሕጋዊ ሰውነታችን ተነጥቆ እንዴት ማስተዳደር እንችላለን ክቡር ሚኒስትር? ለዚህ ጉዳይ እንደደወልክ ገምቻለሁ። ደብዳቤም እኮ ልከናል ክቡር ሚኒስትር፡፡ አዎ። ሁለት ደብዳቤዎች ደርሰውኛል።...