‹‹አንደኛው ተጠርጣሪ ከሌላኛው ተጠርጣሪ ተለይቶ የታሰረበት ምክንያት አልገባንም››
የታሳሪዎች ቤተሰቦች
የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግና የአገሪቱ ርዕሰ ብሔር በአዋጅ የተሰጣቸውን ሥልጣን በመጠቀም በሙስና፣ በሽብርና በተለያዩ ወንጀሎች ተጠርጥረው የተከሰሱና ክርክራቸውን ጨርሰው ተፈርዶባቸው የነበሩ ግለሰቦች እንዲለቀቁ ሲያደርጉ፣ በተመሳሳይ ወንጀል ተጠርጥረው የታሰሩ በርካታ እስረኞች መታለፋቸው ቅሬታ እንዳደረባቸው ለመንግሥት አቤቱታቸውን አቀረቡ፡፡
በቤተሰቦቻቸው አማካይነት ማክሰኞ ግንቦት 21 ቀን 2010 ዓ.ም. በፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ጽሕፈት ቤት ተገኝተው ቅሬታቸውን ያቀረቡት ከስኳር ኮርፖሬሽን፣ ከባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት፣ ከአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣንና ከተለያዩ የመንግሥት ተቋማት በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የታሰሩ ቤተሰቦች ናቸው፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በቤተሰቦቻቸው በኩል ለጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ ባቀረቡት አቤቱታ እንደገለጹት፣ ለእስር የበቁት ከሐምሌ ወር 2009 ዓ.ም. ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት መሆኑንና በወቅቱ ተፈጥሮ የነበረውን ፖለቲካዊ አለመረጋጋት ምክንያት በማድረግ ኢሰብዓዊ በሆነ መንገድ ነው፡፡ ይህንንም በመቃወምና ፍትሕ እንዲሰጣቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አቤቱታቸውን አቅርበዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎች ጉዳዩ የሚመለከተው ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግን እንደሆነ፣ ወደዚያው እንደተመራላቸው ስለነገሯቸው ቤተሰቦቻቸውን ወደ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ አብርሃኑ ፀጋዬ መላካቸውን ቤተሰቦቻቸው በአካል ተገኝተው አስረድተዋል፡፡
ቤተሰቦቻቸው መንግሥት አገራዊ መግባባት እንዲፈጠር እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴና እየወሰደ የሚገኘውን ዕርምጃ እንደሚደግፉ ተናግረው፣ ታሳሪ ቤተሰቦቻቸውም የዚህ አካል እንዲሆኑ ጠይቀዋል፡፡
በወቅቱ የነበሩ የጠቅላይ ዓቃቤ ባለሥልጣናት በመገናኛ ብዙኃን ሲናገሩ ተከሳሾች የተያዙት ማስረጃ ከተሰበሰበና ሁሉ ነገር ከተጠናቀቀ በኋላ መሆኑን የገለጹ ቢሆንም፣ ቤተሰቦቻቸው የታሰሩት ግን ያለምንም ቅድመ ምርመራና ማስረጃ መሆኑን በወቅቱ ፍርድ ቤት ላይ ከመረጋገጡም በላይ፣ አሁንም ክስ ተመሥርቶባቸው እንኳን ክሱን የሚያረጋግጥ አንድም ሰነድ እንዳልተገኘባቸው የክስ ቻርጁን ማየት በቂ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በተደጋጋሚ እንደገለጹትና መንግሥትም እንዲረዳላቸው የሚፈልጉት ያለምንም ማስረጃ ቤተሰቦቻቸው ለእስር በመዳረጋቸው፣ ለእንግልትና ልጆቻቸውንም ማስተዳደር ባለመቻላቸው፣ ለከፋ ጉዳት እየተዳረጉ መሆኑን ማስረዳታቸውን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
ታሳሪ ቤተሰቦቻቸው እንደ ዜጋ ሙስናን ከመንግሥት ጋር በመሆን መታገል የሚፈልጉ እንጂ ሙስናን የሚደግፉ አለመሆናቸውን የሚናገሩት ቤተሰቦቻቸው፣ ይህ የሚቻለው በዘመቻ በሚደረግ አፈሳ ሳይሆን ቅድሚያ ጥናት በማድረግና ንፁኃንን ከሙሰኛው የሚለዩበትን አሠራር በመዘርጋት መሆኑንም አክለዋል፡፡ ሌሎች የሚታወቁና በሥውር የሚንቀሳቀሱ አካላት በፈጸሙት ድርጊት ቤተሰቦቻቸው ሒሳብ ማወራረጃ መሆን እንደሌለባቸው የሚናገሩት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ ለፖለቲካ ፍጆታ ሲባል የታሰሩ በመሆናቸው መንግሥት ልዩ ትኩረት ሰጥቶና መርምሮ ከእስር እንዲለቃቸው ጠይቀዋል፡፡ አብረዋቸው በሙስና ተጠርጥረው ታስረው የነበሩ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ሳይቀሩ መፈታታቸው እንዳስደሰታቸው የገለጹት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ የእነሱ ቤተሰቦች ተለይተው መቅረታቸው ‹‹በብሔራቸው፣ በሃይማኖታቸው ወይስ መንግሥት ሌላ ምክንያት አለው?›› የሚሉ ጥያቄዎችን ለማንሳት እንደተገደዱ አስረድተዋል፡፡
ታሳሪ ቤተሰቦቻቸው ለአገር ያደረጉትን ውለታ ሲያስቡ ክስ ማቋረጥ ብቻ በቂ ሳይሆን፣ የሚያሸልማቸው ተግባር መፈጸማቸው ሥራቸው ህያው ምስክር መሆኑ ለማንም ድብቅ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለአገር መግባባት የሚጠቅም ሥራ እየተሠራ ባለበት በአሁኑ ጊዜ፣ አንዱ ከሌላው ሳይለይ በትብብር የሚንቀሳቀስበት ጊዜ በመሆኑ፣ ተለይተው የታሰሩት ቤተሰቦቻቸው በሥራ ላይ በነበሩበት ጊዜ የነበራቸውን ኃላፊነት ተጠቅመው ለአገር ያበረከቱት አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ከእስር እንዲለቀቁላቸው ደጋግመው መጠየቃቸውን አስረድተዋል፡፡ በተመሳሳይ የወንጀል ድርጊት ተጠርጥረው የታሰሩ ዜጎችን ለይቶ ማሰርና በማረሚያ ቤት መተው፣ አንዱን ዜጋ ከሌላው ዜጋ ማስበለጥና ሌላ ጥላቻ የሚፈጥር በመሆኑ፣ ሁሉንም እኩል በማየት በሕግ ፊት እኩል መሆናቸውን መንግሥት እንዲያረጋግጥላቸውም ጠይቀዋል፡፡
መንግሥት እያከናወነ ያለውን ሪፎሮም በበጎ የሚያዩት በመሆኑም፣ የታሰሩ ቤተሰቦቻቸው ከእስር ተፈትተው ከመንግሥት ጎን በመቆም ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉና የሚመለከተው የመንግሥት አካል አቤቱታቸውን በአንክሮ ተመልክተው፣ አፋጣኝ ምላሽ እንደሚሰጧቸው በመተማመን አቤቱታቸውን ማቅረባቸውን አስታውቀዋል፡፡ አቤቱታቸውን ለማቅረብ ማክሰኞ ግንቦት 21 ቀን 2010 ዓ.ም. በጽሕፈት ቤታቸው ሲገኙ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕጉ ስብሰባ ላይ መሆናቸውን እንደገለጹላቸውና በጸሐፊያቸው በኩል አቤቱታው እንደሚደርሳቸውና ምላሽ እንደሚሰጧቸውም ቃል እንደገቡላቸው ተናግረዋል፡፡