የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኮርፖሬሽን ለሁለት ከተከፈለ በኋላ ከነሐሴ ወር 2007 ዓ.ም. ጀምሮ፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎትን ለመምራት ሁለተኛው ዋና ሥራ አስፈጻሚ በመሆን ተመድበው የነበሩት አቶ ጎሳዬ መንግሥቴ በሌላ ኃላፊ ተተኩ፡፡
አቶ ጎሳዬ የተተኩት የቀድሞው የኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን አገር አቀፍ ኤሌክትሪክ አቅርቦት ሥራ አስፈጻሚ በነበሩት አቶ ሽፈራው ተሊላ ነው፡፡
በተቋሙ ከ20 ዓመታት በላይ በተለያዩ የሥራ ዘርፎችና ኃላፊነት የቆዩት አቶ ሽፈራው የኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው እንዲሠሩ የተወሰነው ግንቦት 14 ቀን 2010 ዓ.ም. ቢሆንም፣ ሥራ የሚጀምሩት ግን ከግንቦት 21 ቀን 2010 ዓ.ም. መሆኑን፣ ግንቦት 20 ቀን 2010 ዓ.ም. በአገልግሎቱ የቦርድ ሰብሳቢ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂነር) ተፈርሞ ወጪ የተደረገው ደብዳቤ ይገልጻል፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዳይሬክተሮች ቦርድ ግንቦት 14 ቀን 2010 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ፣ ጡረታ በሚወጡት አቶ ጎሳዬ ምትክ ‹‹ማን ይመድብ?›› ተብሎ የተለያዩ ሐሳቦች ተነስተው የነበረ ቢሆንም፣ አቶ ሽፈራው የከፍተኛ ኃላፊዎችን ማለትም የተወሰኑ የቦርድ አባላትን ይሁንታ በማግኘታቸው ሊመድቡ መቻላቸው ታውቋል፡፡ አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች አቶ ሽፈራው ለቦታው እንደማይመጥኑ በመጠቆም፣ በዘርፉ ብዙ ልምድ ያላቸውና በአመራርነት ሰፊ ዕውቀት ያላቸው መመደብ ሲገባቸው፣ በዝምታ መታለፉ ተገቢ እንደልሆነ ገልጸዋል፡፡ ምናልባት ቀደም ባሉ ዓመታት ግለሰቡ ከነበሩበት ኃላፊነት ተነስተው በሌላ ቦታ እንዲሠሩ ተደርገው ስለነበር፣ ለሱም ማካካሻ ሳይሆን እንደማይቀር አስተያየት ሰጪዎቹ ግምታቸውን ተናግረዋል፡፡
አቶ ሽፈራው ስላላቸው የሥራ ልምድና ስለተመደቡበት የሥራ ኃላፊነት ያላቸውን የሥራ አመራር ዕቅድ ማብራሪያ እንዲሰጡ በተደጋጋሚ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡