በጋምቤላ ክልል በተቀሰቀሰ ግጭት ከ20 በላይ ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተሰማ፡፡ ከሐሙስ ጥር 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ጀምሮ ተባብሶ በቀጠለው ግጭት በክልሉ ውጥረት ነግሷል፡፡
ከጋምቤላ ክልል የተገኙ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ በግለሰቦች መካከል የተነሳው አለመግባባት መልኩን ቀይሮ በኑዌርና በአኙዋ ብሔረሰቦች መካከል የከፋ ግጭት አስከትሏል፡፡
በዚህ ግጭት ከ20 በላይ ሰዎች ሕይወት እንዳለፈና በርካቶች ለአካል ጉዳት እንደተዳረጉ የአይን እማኞች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በንብረት ላይም ጉዳት እየደረሰ መሆኑ ታውቋል፡፡ በጋምቤላ ከተማ የተነሳው ግጭት ሁለቱ ብሔረሰቦች የሚኖሩባቸው ወረዳዎች ጭምር የተሸጋገረ ሲሆን፣ ዓርብ ጥር 20 ቀን 2008 ዓ.ም. ደግሞ በጋምቤላ ከተማ በሚገኘው ማረሚያ ቤት ጭምር ግጭቱ ተከስቶ የበርካታ ታራሚዎች ሕይወት ማለፉ ተሰምቷል፡፡
በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት በጋምቤላ ከተማ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች፣ የንግድና የትምህርት ተቋማት በሙሉ መዘጋታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ግጭቱን ለማብረድ የመከላከያ ሠራዊትና የፌዴራል ፖሊስ ኃይል ተሰማርቷል፡፡ ለሥራ ጉዳይ አዲስ አበባ የነበሩት የጋምቤላ ፕሬዚዳንት አቶ ታትሉዋክ ቱትና ምክትል ፕሬዚዳንቱ ኢንጂነር ኦሌሮ ኦፒዮ የመጡበትን ጉዳይ አቋርጠው ወደ ጋምቤላ ተመልሰዋል፡፡
የጋምቤላ ፕሬዚዳንት አቶ ጋትሉዋክ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የግጭቱ መንስዔ በመጣራት ላይ ነው፡፡ የጉዳቱን መጠን ለማወቅ መረጃ እየተሰበሰበ በመሆኑ አሁን [ባለፈው ዓርብ] ይህ ያህል ነው ለማለት እንደማይቻል ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡
አምስት ነባር ብሔረሰቦች ባሏትና በተፈጥሮ ሀብት በበለፀገችው ጋምቤላ፣ ከአምስቱ ብሔረሰቦች መካከል በተለይ በኑዌርና በአኝዋ መካከል በተለያዩ ጊዜያት ግጭቶች ተከስተዋል፡፡
በሁለቱ ብሔረሰቦች መካከል የሚነሱት ግጭቶች የሥልጣን ጥያቄ ያዘሉ መሆኑን ከክልሉ የሚወጡ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት በክልሉ ውጥረት በመንገሡ ነዋሪዎች ከፍተኛ ሥጋት ላይ መውደቃቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡