‹‹የሱፍ አበባ›› ይባላል፤ በደራሲ ሀብታሙ አለባቸው ተጽፎ በሊትማነ ቡክስ የታተመውና ጭብጡን በብርሃነ መስቀል ረዳ የፖለቲካ ሰብዕናና ሕይወት ዙሪያ ያደረገው አዲስ መጽሐፍ፡፡
የሱፍ አበባ የኢሕአፓ ከፍተኛ አመራሮችን በተለይም የብርሃነ መስቀል ረዳን ፖለቲካዊ ሥነ ልቦና እና ቁመና እንዲሁም ፖለቲካዊ እሳቤው ምን ይመስል እንደነበር የሚተነትን ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ብርሃነ መስቀል ረዳ ከነጌታቸው ማሩ፣ ዘሩ ኩኽሽን፣ ክፍሉ ታደሰና ዶክተር ተስፋዬ ደበሳይ ጋር በከተማ ትጥቅ ትግል ዙሪያ የነበረውን የከረረ ቅራኔ ያስቃኛል፡፡ 379 ገጾች ያሉት ይህ መጽሐፍ ሊትማን ቡክስ በ91 ብር ያከፋፍለዋል፡፡
ደራሲው አቶ ሀብታሙ አለባችው ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ፖለቲካዊ ትንታኔዎችን በእንግሊዝኛ ቋንቋ በመጻፍና በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮች ተሳትፎ በማድረግ ይታወቃሉ፡፡ በተጨማሪም የተለያዩ አፍሪካ አገሮች የኢትዮጵያ ታሪክና ፖለቲካን የተመለከቱ አካዴሚክ ጥናታዊ ሥራዎቻቸውን በማቅረብ ቆይተዋል፡፡
ታሪክ ቀመስ ፖለቲካዊ ልቦለዶችን በመጻፍ ረገድ ይህ ሦስተኛው ሥራቸው ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም በኤርትራዊው ፖለቲካዊ ሥነ ልቦና ዙሪያ የጻፉት ‹‹አውሮራ››፣ በኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ሕይወት ዙሪያ የሚያጠነጥነው ‹‹የቄሳር እንባ›› የተሰኘው ሁለተኛውን መጽሐፋቸውን ማሳተማቸው ይታወቃል፡፡
‹‹ኢስት ኦፍ ኤደን›› ወደ አማርኛ ተመለሰ
ለምርጥ የሥነ ጽሑፍ ሥራ የሚሰጠውን የፑልቲዘርና የኖቤል ሽልማት ተሸላሚው የአሜሪካዊው ዕውቅ ደራሲ የጆን ሰቴንቤክ ‹‹ኢስት ኦፍ ኤደን›› የተባለው መጽሐፍ ተተርጉሞ ገበያ ላይ ዋለ፡፡
መጽሐፉን ‹‹ከገነት በስተ ምሥራቅ›› በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ የተረጐሙት አቶ ጌታቸው አሻግሬ ናቸው፡፡
ኢስት ኦፍ ኤደን የማንንም ሰው ስሜት የሚኮረኩር፣ የምድራዊው ዓለማችንን እውነተኛ ገጽታ የሚያሳይና የሰው ልጅ ባህሪ ስለሆኑት ክፋትና ደግነት ተአማኝና ተጨባጭ በሆነ አቀራረብ የተደረሰ በመሆኑ ተተርጉሞ ለአንባቢያን ቢቀርብ በሚል ጽኑ ፍላጎት ተነሳስተው መተርጐማቸውን ተርጓሚው በመቅድማቸው ላይ ገልጸዋል፡፡
መጽሐፉ የደራሲው እምቅ ችሎታ የታየበት፣ ጊዜ የማይሽረው፣ የማይረሱ ገፀ ባህሪያት የሚታዩበት፣ ስለማንነትና ስለፍቅር ገለጻው የገሃዱ ዓለም ተቀባይነት ያለውና ዕውቅ ከሆኑት የአሜሪካ ልብ ወለዶች አንዱ ነው፡፡ ደራሲ ጆን ስቴንቤክ እ.ኤ.አ. በፌብርዋሪ 27 ቀን 1902 በአሜሪካ በካሊፎርኒያ ግዛት ሳሊናስ በተባለው ቦታ ተወልዶ በዲሴምበር 20 ቀን 1968 ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡
የአማርኛው ትርጉም 500 ገጾች ያሉትና በ90 ብር ለገበያ የቀረበ ሲሆን አከፋፋዩ ክብሩ የመጻሕፍት መደብር መሆኑ ታውቋል፡፡