Thursday, June 8, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናጦማሪያኑ ለቀረበባቸው የይግባኝ አቤቱታ መቃወሚያ አቀረቡ

ጦማሪያኑ ለቀረበባቸው የይግባኝ አቤቱታ መቃወሚያ አቀረቡ

ቀን:

የሽብር ድርጊት ወንጀል በመፈጸም ተጠርጥረው ክስ ተመሥርቶባቸው ሲከራከሩ ከርመው መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ የተሰናበቱት አምስት ጦማሪያን፣ ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ባቀረበባቸው የይግባኝ አቤቱታ ላይ ጥር 27 ቀን 2008 ዓ.ም. መቃወሚያቸውን አቀረቡ፡፡ ከጦማሪያኑ አንዱ የጥፋተኛነት ውሳኔ ሳይሰጥበት ይግባኝ መደረጉ አግባብ እንዳልሆነ አመልክቷል፡፡ ከሳሽ የፌዴራል ከፍተኛ ዓቃቤ ሕግ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተከሳሾቹን በነፃ ያሰናበታቸው ያቀረበውን የሰውና የሰነድ ማስረጃ ሳይመረምር በማለፍ መሆኑን በመግለጽ፣ ውሳኔውን ተቃውሞ ይግባኝ ማቅረቡን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ዓቃቤ ሕግ በይግባኝ አቤቱታው ለይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት እንደገለጸው፣ ተከሳሾቹ በህቡዕ ተደራጅተው ለሽብርና ለአመፅ መዘጋጀታቸውን የሚያስረዳ የሰነድ ማስረጃ አቅርቦ ሳይታይ ታልፏል፡፡ እያንዳንዳቸው በህቡዕ በመደራጀትና የሥራ ክፍፍል ማድረጋቸው የተገለጸ ቢሆንም ይኼም ታልፏል፡፡ እንዲሁም ተከሳሾቹ በሽብር ቡድን ውስጥ መሳተፋቸውን የሚገልጽ ማስረጃ የቀረበባቸው ቢሆንም፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሽብርተኛ ተብሎ ሳይፈረጅ ሽብርተኛ መባሉ አግባብ አይደለም በማለት ተከሳሾቹ ያቀረቡትን መቃወሚያ ተቀብሎ የእሱ ማስረጃ እንደታለፈበት በመግለጽ መቃወሚያውን አቅርቧል፡፡ ስለመደራጀታቸው፣ ሥልጠና ስለመውሰዳቸው፣ መዘጋጀታቸውንና ማሴራቸውንም የሚያስረዳ ሰነድ ቀርቦባቸው ፍርድ ቤቱ በአግባቡ እንዳልመዘነለት ዓቃቤ ሕግ በይግባኝ አቤቱታው ለይግባኝ ሰሚው ችሎት አቅርቧል፡፡ ጦማሪያኑ በጠበቃቸው በአቶ አመሐ መኮንን አማካይነት ባቀረቡት የመቃወሚያ ክርክር ለይግባኝ ሰሚው ችሎት እንዳስረዱት፣ የሥር ፍርድ ቤት በጥቅሉ የሽብር ቡድን ብሎ በዓቃቤ ሕግ የተጠቀሰን ክስ የቡድኑን ስም እንዲገልጽ ወይም ከሌሎች የሚለይበትን ሁኔታ ገልጾ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ ዓቃቤ ሕግ በፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መሠረት ባያቀርብም ፍርድ ቤቱ ግን ክሱን የሚደግፍ ብይን በመስጠቱ ተቃውሞ መቅረቡ ተገቢ አለመሆኑን አስረድተዋል፡፡ ሌላው የሥር ፍርድ ቤት ማስረጃውን ሳይመረምር ክሱን ውድቅ እንዳደረገበት ዓቃቤ ሕግ በማመልከቻው የጠቀሰው፣ ተከሳሾቹ በህቡዕ ተደራጅተውና የሥራ ክፍፍል ማድረጋቸውን ገልጾ እያለ እንደታለፈበት የገለጸውን በሚመለከት ትክክል አለመሆኑን አስረድተዋል፡፡ በተደጋጋሚ እያንዳንዱ ተከሳሽ በቡድኑ ውስጥ ማን ምን የሥራ ድርሻ እንዳለው ዓቃቤ ሕግ ጠቅሶ እንዲያቀርብ፣ ወይም ክሱን እንዲያሻሽል ተነግሮት ተግባራዊ ባለመደረጉ ከክሱ ዝርዝር ውስጥ መሰረዙ ቅር የሚያሰኝ እንዳልሆነ በመግለጽ ተከራክረዋል፡፡ ዓቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ የፀረ ሽብር አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ (3)ን ጠቅሶ ተከሳሾቹ ማሴራቸውን፣ መዘጋጀታቸውንና ማቀዳቸውን የሚገልጽ የሰነድ ማስረጃ አቅርቦ የሥር ፍርድ ቤት ሳይመረምር ያለፈበት መሆኑን በሚመለከትም አስረድተዋል፡፡ በተከሳሾቹ ላይ ተገኘ የተባለው ማስረጃ ዓቃቤ ሕግ እንደገለጸው ማቀዳቸውን፣ መዘጋጀታቸውንና ማሴራቸውን የሚያስረዳ ሳይሆን፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 29 የተፈቀደላቸውን ሐሳባቸውን በነፃነት የመግለጽ መብታቸውን የሚያሳይ፣ መንግሥት ሐሳቡን በነፃነት የሚገልጸውን እንደሚያስርና እንደሚከለክል የሚገለጸውን ወይም የሚነገረውን የሚያስተባብልና ትክክለኛ አካሄድ መሆኑን የሚገልጽ እንደሆነ ገልጾ ብይን መስጠቱ፣ ተገቢና ትክክል በመሆኑ ቅሬታ ሊቀርብበት እንደማይችል ሰፊ ማብራሪያ በመስጠት መቃወሚያቸውን አሰምተዋል፡፡ ይግባኝ የተባለባቸው ጦማሪያን ሶሊያና ሽመልስ (በሌለችበት)፣ በፍቃዱ ኃይሉ (በሥር ፍርድ ቤት ተከላከል የተባለ)፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ አጥናፉ ብርሃኔና አቤል ዋበላ ናቸው፡፡ በፍቃዱ ኃይሉ በሥር ፍርድ ቤት ተከላከል ተብሎ በሒደት ላይ እያለ የወንጀል ሕግ 181 ድንጋጌን በመታለፍ በተመሳሳይ የክስ ጉዳይ ሁለት የተለያዩ ችሎቶች ላይ እንዲቀርብና እንዲከራከር መደረጉ፣ ሕግን የጣሰ አካሄድና እስከዛሬም ተቀባይነት ያላገኘ አሠራር በመሆኑ ውድቅ እንዲደረግለት ለይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት አቤቱታ አቅርቧል፡፡ የሁለቱን ወገኖች ክርክር የሰማው ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቤት ክርክሩን መርምሮ ውሳኔ ለመስጠት፣ ለመጋቢት 16 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ከቀጣዩ ዓመት በጀት ውስጥ 281 ቢሊዮን ብሩ የበጀት ጉደለት ነው ተባለ

ለቀጣዩ በጀት ዓመት ከቀረበው 801.65 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ በጀት...

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው አሠራር ወጣ ያለውን ‹‹የወደፊት ግብይት›› ሥርዓት በይፋ አስጀመረ

የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ከተለመደው የማገበያየት ተግባሩ ወጣ ያለና በኢትዮጵያ...

የባንክ ማቋቋሚያ መሥፈርት እንደሚጠነክር ሚኒስትሩ ተናገሩ

 ባንኮች ስለውህደት እንዲያስቡም መክረዋል በኢትዮጵያ ውስጥ ባንክ ለማቋቋም የሚያስፈልገው መሥፈርት...