በቅርቡ በኬንያ ግድብ ተደርምሶ በደረሰ ጥፋት የተደናገጠው የኢትዮጵያ መንግሥት፣ በአገሪቱ የሚገኙ ሁሉም ግድቦች ያሉበት ነባራዊ ሁኔታ ተጠንቶ እንዲታወቅ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
የውኃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር የግድቦች ቆጠራና ደኅንነት ሁኔታ የሚያጠና ኩባንያ ለመምረጥ ያወጣው ጨረታ፣ ረቡዕ ግንቦት 29 ቀን 2010 ዓ.ም. በይፋ ይከፈታል፡፡
ጨረታ የወጣው ለአገር በቀል አማካሪ ድርጅቶች ብቻ ነው፡፡ ሥራውም በተለያዩ ምክንያቶች የተገነቡ ግድቦችን መቁጠር፣ ደኅንነታቸውን፣ እንዲሁም ችግር ቢገጥማቸው የሚንደረደረው ውኃ በሰውና በንብረት ላይ ሊያደርስ የሚችለውን ጉዳት ማወቅ ያካትታል፡፡
ከጥቂት ሳምንታት በፊት በኬንያ ከናይሮቢ 190 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሶላይ ከተማ አቅራቢያ ለመስኖ ሥራ የሚያገለግል ግድብ ተደርምሶ፣ ከ40 በላይ የሰው ሕይወት መቅጠፉ ይታወሳል፡፡
የግድቡ መደርመስ ከሁለት ሺሕ በላይ ሰዎችን ቤት አልባ ሲያደርግ፣ ሰፊ ቦታ የሚሸፍን ማሳ አጥፍቷል፡፡ ይህ ክስተት ለኢትዮጵያ መንግሥት እንደ ማንቂያ ደወል ሆኗል፡፡ በኢትዮጵያ ተመሳሳይ ድርጊት ቢያጋጥም ሊደርስ የሚችለውን ጥፋት፣ ጥፋቱ ከመድረሱ በፊት ጥንቃቄ ለማድረግ መረጃ መያዝ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ሚኒስቴሩ ጨረታ ማውጣቱ ተገልጿል፡፡
በኢትዮጵያ እስካሁን ከ100 በላይ የመስኖና የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድቦች እንዳሉ ይነገራል፡፡
ነገር ግን ከባድ ዝናብ በሚዘንብበትና በዝናቡ ምክንያት የመደርመስ አደጋ ቢያጋጥም፣ በታችኛው ተፋሰስ አካባቢ የሚገኙ ዜጎች ዕጣ ፈንታና ሊደርስ የሚችል የንብረት ውድመት እስካሁን በጥናት የተደገፈ መልስ እንደሌለ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡