– ፀረ ሙስና ኮሚሽን ግዙፍ ችግሮች ተጠቁመውበታል
- በሙስና ሀብት አካብተው ኮሚሽኑን የሚለቁ አሉ
- ለኮሚሽኑ የሚደርሱ ጥቆማዎች ለተጠቋሚው ይደርሳሉ
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በተመረጡ የፌዴራልና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ክፍላተ ከተሞች ባካሄደው ሱፐርቪዥን ያገኛቸውን ግዙፍ ችግሮች ይፋ አደረገ፡፡ ፀረ ሙስና ኮሚሽን ከመልካም አስተዳደር ችግር ይልቅ የወንጀል ይዘት ያላቸው ችግሮች ተጠቁመውበታል፡፡
የፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ላይ የፓርላማው ልዩ የክትትልና የቁጥጥር ቡድን ከለያቸው ችግሮች መካከል በዘርፉ መልካም አስተዳደር አለመስፈኑ፣ አድሎአዊ፣ ፀረ ዴሞክራሲያዊ፣ ጤናማ የአመራርና የሠራተኛ ግንኙነት ያልተፈጠረ መሆኑ ይገኝበታል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ተቋሙን በቅንነት የሚያገለግሉና የሚታገሉ ሠራተኞችን ከቦታ ወደ ቦታ እንዲዘዋወሩ ማድረግ የሚለውም ተወስቷል፡፡ በተጨማሪም አመራሩን የሚታገሉ ሠራተኞች ተቋሙን ለቀው እንዲወጡ ጫና መፍጠር እንደሚገኝበትም ፓርላማው ይፋ አድርጓል፡፡
የሚቋረጡ የክስ ፋይሎች መኖራቸውን፣ የሥነ ምግባር መኮንኖች የሙስና መዝገቦች ላይ ተገቢ ምርመራ እንዳይደረግ ጫና እንደሚያደርጉ፤ በሙስና ሀብት አካብተው ሥራ የሚለቁ ሠራተኞች መኖራቸው፣ እንዲሁም ኮሚሽኑ እነዚህን ሠራተኞች የማይከታተላቸው መሆኑን ፓርላማው ይፋ አድርጓል፡፡
የሪፎርም ሥራ ከሪፖርት ባለፈ ተግባር ላይ የሌለና አመራሩ እየመራው አለመሆኑ፣ በኮሚሽኑ ላይ ቅሬታ ያላቸው ዜጎች አቤቱታ የሚያቀርቡበት ቦታና ገለልተኛ አካል አለመኖሩን ጠቅሷል፡፡
በኮሚሽኑ በሙስና የሚጠረጠሩ ሠራተኞች መኖራቸውና በእነዚሁ ግለሰቦች ላይ የማጣራት ሥራ እየተሠራ አለመሆኑ፣ እንዲሁም ለተቋሙ የሚቀርቡ ጥቆማዎችን ሚስጥር አለመጠበቅና ጉዳዩ ሳይጣራ ለተጠቋሚው ሚስጥር አውጥቶ መስጠት እንዳለ የክትትል ቡድኑ ለምክር ቤቱ ይፋ አድርጓል፡፡
የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በሕግ የተቋቋመው ሥራ አስፈጻሚውን መንግሥት በመቆጣጠር መልካም አስተዳደር በአስፈጻሚው መዋቅር ውስጥ እንዲሰፍን ማድረግ ሆኖ ሳለ፣ ራሱ በመልካም አስተዳደር ችግሮች ውስጥ መዘፈቁና የወንጀል ይዘት ያላቸው ተግባራት የሚፈጸሙበት ተቋም መሆኑ በፓርላማው ሪፖርት ተረጋግጧል፡፡ በሌሎች አገልግሎት ሰጪ የአስፈጻሚው መዋቅሮች ውስጥም ያለው ችግር ይፋ ሆኗል፡፡ ዝርዝሩን በገጽ 6 ይመልከቱ፡፡