በአከራይ ተከራይና በሪል ስቴት ዘርፍ የተንሰራፋውን የተመሰቃቀለ የመኖሪያ ቤቶች ግብይት መልክ ለማስያዝ የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ ከተጠናቀቀ ሁለት ዓመት ቢያስቆጥርም፣ እስካሁን ለሚኒስትሮች ምክር ቤት አለመቅረቡ ታወቀ፡፡
የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር በተናጠል ያዘጋጃቸው የአከራይ ተከራይ ግብይት፣ የሪል ስቴት ግብይትና የመንግሥት ቤቶች አስተዳደር በሚመለከት ያዘጋጃቸው ሦስት አዋጆች ተጠቃለው በአንድ አዋጅ እንዲዘጋጁ ትዕዛዝ የተሰጠው በ2005 ዓ.ም. ነበር፡፡
በዚህ መሠረት የሚኒስትሩ የሕግ ዳይሬክቶሬት ሦስቱ አዋጆችን በአንድነት አሰባጥሮ ለውይይት በማቅረብ ጠቃሚ ግብዓት ሲሰበስብ ቆይቷል፡፡
ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የሚኒስቴሩ ባለሥልጣን ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ሦስቱን ጉዳዮች በያዘው ረቂቅ አዋጅ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ተካሂዶ የተገኙ ጠቃሚ ሐሳቦችና ፍትሕ ሚኒስቴር የሰጠው አስተያየት ተካቶ የመጨረሻው ረቂቅ አዋጅ ከተዘጋጀ ሁለት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ያልቀረበበትን ምክንያት እንደማያውቁ፣ ረቂቅ አዋጅ ፀድቆ ሥራ ላይ ቢውል መሠረታዊ ለውጥ ያመጣ እንደነበር እኚሁ ባለሥልጣን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
ነገር ግን የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከዚህ ሁሉ ጊዜ በኋላም ጥናቱ እንዳላለቀ ነው የሚናገሩት፡፡ በቅርቡ የከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስትር ዴኤታ ሆነው የተሾሙት አቶ ጌታቸው ኃይለ ማርያም፣ ሪፖርተር በሪል ስቴት ዘርፍ የተፈጠረውን የግብይት መመሰቃቀልና በቤት አከራዮች በየጊዜው እየጨመረ ለሚገኘው የመኖሪያ ቤት ኪራይ ዋጋ ጭማሪ መልስ የሚሰጥ ረቂቅ አዋጅ መዘጋጀቱን፣ ነገር ግን ሕጉን ለመንግሥት ማቅረብ ባለመቻሉ ጉዳዩ በነዋሪዎች ላይ ከፍተኛ ችግር እያስከተለ በመሆኑ ምን እያደረጋችሁ ነው? የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው ነበር፡፡ ‹‹ጥናቱ ባለመጠናቀቁ ነው ለመንግሥት ያልቀረበው፡፡ ጥናቱ ሲጠናቀቅ ረቂቅ ሕጉ ለመንግሥት እንደሚቀርብና ከፀደቀም ተግባራዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ይገባል፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ሚኒስቴሩ ይህንን ረቂቅ አዋጅ ያዘጋጀው እየናረ ያለውን የመኖሪያ ቤቶች ኪራይ ዋጋ ሥርዓት ለማስያዝ ሕጉን ማውጣት አስፈላጊ ነው ተብሎ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የሚኒስቴሩ ባለሙያዎች ሲንጋፖርን ጨምሮ የተለያዩ አገሮችን ልምድ መሠረት በማድረግ፣ በኪራይ የሚቀርቡ መኖሪያ ቤቶች እንደሚያሟሉት የአገልግሎት ደረጃ የዋጋ ደረጃ ተዘጋጅቷል፡፡ ባለፈው ዓመት አጋማሽ ይህ ረቂቅ አዋጅ እየተጠናቀቀ በመሆኑ ሥራ ላይ እንደሚውል በይፋ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቶም እንደነበር ይታወሳል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ይህ አዋጅ ተግባር ላይ ሲውል በሪል ስቴት ዘርፍ የተንሰራፋው ሕገወጥ ግብይት ሥርዓት እንደሚያሲዝ ተመልክቷል፡፡ በመንግሥት ቤቶች ላይ የሚታየው ሕገወጥ አሠራር በዚህ አዋጅ ምላሽ ያገኛል ተብሎ ነበር፡፡
ነገር ግን ይህ አጠቃላይ ሕጋዊ ጽንሰ ሐሳብ የተነሳው ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ ቢሆንም፣ አሁንም በ2008 ዓ.ም. የተጠበቀው ነገር ወደታች እንዳልወረደ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡