አርበኞች ግንቦት ሰባትን ለመቀላቀል ከአዲስ አበባ ወደ ኤርትራ በመጓዝ ላይ እያሉ ድንበር ላይ መያዛቸው የተገለጸው፣ የሰማያዊ ፓርቲ አራት አባላት የተመሠረተባቸውን ክስ እንዲከላከሉ ብይን ተሰጠ፡፡
የፓርቲው አመራሮች የነበሩት አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ፣ ወይዘሪት እየሩሳሌም ተስፋው፣ አቶ ፍቅረ ማርያም አስማማውና አቶ ደሴ ካህሳይ፣ የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ የመሠረተባቸውን ክስ በሰነድና በሰዎች ምስክሮች አስረድቷል ያለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 14ኛ ወንጀል ችሎት እንዲከላከሉ ብይን ሰጥቷል፡፡
ተከሳሾቹ ክሳቸውን እየመረመረው የሚገኘው ችሎት እንዲቀየርላቸው ያመለከቱ ቢሆንም፣ ማመልከቻቸው ታልፎ ብይን በመስጠት የመከላከያ ምስክር እንዳላቸውና እንደሌላቸው ለችሎቱ እንዲያስረዱ ተጠይቀዋል፡፡
ተከሳሾቹ ለፍርድ ቤቱ እንዳስረዱት፣ 200 የሰው ምስክሮችና የሰነድ ማስረጃዎችን በማቅረብ የቀረበባቸውን ክስ ይከላከላሉ፡፡ ፍርድ ቤቱ የመከላከያ ምስክርነታቸውን ለመስማት ለመጋቢት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡