በሕገወጥ መንገድ መሬት ወረው መኖርያ ቤት ገንብተዋል በሚል ምክንያት የተፈናቀሉ የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ነዋሪዎች፣ ለከፍተኛ ችግር መዳረጋቸውን በመግለጽ መንግሥት እንዲደርስላቸው ጠየቁ፡፡
በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ አራት ቀጣና አምስት ከክራውን ሆቴል ጀርባ ልዩ ስሙ ሰሪቲ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ የተፈናቀሉ 336 አባወራዎች፣ በወኪሎቻቸው አማካይነት ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ድሪባ ኩማ በጻፉት ደብዳቤ፣ ያለምንም በቂ ምክንያት ቤቶቻቸው በመፍረሳቸው ቤተሰብ ይዘው ለአደጋ መጋለጣቸውን አመልክተዋል፡፡
ተፈናቃዮቹ በጻፉት ደብዳቤ ሰኔ 27 ቀን 2008 ዓ.ም. ያለምንም ማስጠንቀቂያ ቦታው ለምንም ጉዳይ ሳይፈለግ በግብረ ኃይል እንዲፈርስ ተደርጓል ብለዋል፡፡ ‹‹ምንም በማናውቀው ጉዳይ ያፈራነው ሀብትና ንብረት ወድሞብን፣ ከመንግሥት ጋር በትብብር ስናለማ የነበረው መሠረተ ልማት ፈርሶብን ለከፍተኛ ችግር ተዳርገናል፡፡ ላለፉት ሁለት ዓመታት መሄጃ ስለሌለንም ላስቲክ ወጥረን እዚያው እየኖርን ነው፤›› በማለት ተፈናቃዮቹ የደረሰባቸውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ለከንቲባው በጻፉት ደብዳቤ ገልጸዋል፡፡
የተፈናቃዮቹ ኮሚቴ አባል መሪጌታ ቤዛ ካሳዬ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ቤቶቹ ከመፍረሳቸው በፊት በ2007 ዓ.ም. በወረዳው ሰነድ አጣሪ ኮሚቴ ተመዝግቦና የባለቤትነት ጉዳይ ተጣርቶ ሰነዶችን በወረዳና በክፍለ ከተማ ተመሳክሮ ከሽንሻኖ ክፍል በካርታ ልኬት ተዘጋጅቶ ነበር፡፡
‹‹የባለቤትነት ካርታ ሊሰጠን እንቅስቃሴ ቀጥሎ እያለ ምንም በማናውቀው ጉዳይ ሰኔ 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ቤቶቻችን በግብረ ኃይል ተንደዋል፤›› በማለት መሪጌታ ቤዛ አስረድተዋል፡፡
ተፈናቃዮች ለከንቲባው በጻፉት ደብዳቤ፣ ‹‹እንደ ኢትዮጵያዊነታችን መፍትሔ ይሰጠን፡፡ በመኖርያ ቤት ዕጦት ለአደጋ መጋለጣችን ታውቆ ቦታችን ይፅና ወይም መኖርያ ቤት ይሰጠን፤›› ሲሉ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤትና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ አያና አዳሙ አስተያየት እንዲሰጡ የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡