የሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ማዕከላዊ ኮሚቴ ረቡዕ ሰኔ 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴን ለመሠረታዊ የኢኮኖሚ ችግር ጊዜያዊ መፍትሔ ላይ ከማተኮር ይልቅ ዘላቂ መፍትሔ ሊሰጥ ይገባ ነበር ሲል ወቀሰ፡፡
ሕወሓት በመግለጫው፣ ‹‹የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ማየት የነበረበት መሠረታዊ ጉዳይ አሁን ገጥሞን ላለው የኢኮኖሚ ችግር ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለግ መሆን ሲገባዉ፣ ችግሩ ባስከተላቸው ውጤቶችና ለጊዚያዊ መፍትሔዎች ቅድሚያ መስጠቱ አንድ ጉድለት እንደሆነና፣ ዘላቂው መፍትሔ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መስመራችን በግልጽ የለያቸውን የልማት አቅሞቻችን፣ ማለትም መላው ሕዝባችን፣ መንግሥትና የግል ባለሀብቱን በማደራጀት ርብርብ እንዲያደርጉ ትኩረት መስጠት አልቻለም፤›› ብሏል፡፡
ድርጅቱ ለሁለት ቀናት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባም የኢሕአዴግ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ትላልቅ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሙሉ በሙሉ ወይንም በከፊል ለመሸጥ ያስተላለፋቸውን ውሳኔዎች እንደሚቀበል፣ ነገር ግን አፈጻጸሙ ላይ ውይይትና ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት አስታውቋል፡፡
የኢትዮ ኤርትራን የድንበር ኮሚሽን ውሳኔና የአልጄርሱ ውይይት በሚመለከት የተላለፈውም ውሳኔ ከአገሪቱ የሰላም ፖሊሲ ጋር የተጣጣመ በመሆኑ ተገቢና ወቅታዊ ነው ብሏል፡፡ ‹‹አፈጻጸሙን በሚመለከት ግን አገራችን ከሌሎች ጎረቤት አገሮች ጋር ካሏት የአዋሳኝ ድንበር ጉዳዮች አንፃር ጭምር እጅግ ከፍ ያለ ትርጉም ያለዉ በመሆኑ፣ በከፍተኛ ጥንቃቄ ሊታይ እንደሚገባዉ አፅንኦት ሰጥቶ ተወያይቷል፤›› ሲል አስታውቋል፡፡
ይሁንና ማዕከላዊ ኮሚቴው፣ ‹‹በኢትዮ ኤርትራ ዘላቂ ሰላም ጉዳይም ሆነ ከመንግሥት የልማት ድርጅቶች ጋር በተያያዘ የተወሰኑ ውሳኔዎች ወደ ኢሕአዴግ ምክር ቤት ሳይቀርቡ፣ አጋር ድርጅቶች ሳይሳተፉበትና የሚመልከታቸው አካላት በዝርዝር ሳይወያዩበት እንደመጨረሻ ውሳኔ ተወስዶ ለሕዝብ ይፋ መደረጉ አንድ ጉድለት እንደሆነ ማዕከላዊ ኮሚቴዉ ደምድሟ፤›› ሲል በመግለጫው አትቷል፡፡
ድርጅቱ አክሎም፣ ‹‹በአሁኑ ወቅት በኢሕአዴግ ደረጃ እየተደረጉ ያሉ የኢሕአዴግን ሕገ ደንብና ተቋማዊ አሠራር ያልተከተሉ የአመራር ምደባዎች እንዲታረሙ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ይጠይቃል፤›› በማለት፣ ‹‹ወቅታዊ ሁኔታውን በፍጥነት ለማየትና ለመገምገም የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴና ምክር ቤት አስቸኳይ ሰብሰባ እንዲጠራ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ይጠይቃል፤›› ብሏል፡፡