በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከመሬት ጋር በተያያዘ ሙስና ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩ 85 አመራሮችና ሠራተኞች በቁጥጥር ሥር ዋሉ፡፡ የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጋር በመሆን የካቲት 18 ቀን 2008 ዓ.ም እና የካቲት 21 ቀን 2008 ዓ.ም. ተጠርጣሪዎቹን በቁጥጥር ሥር አውሏል፡፡
የካቲት 18 ቀን 2008 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር የዋሉት 62 ተጠርጣሪዎች፣ የካቲት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሁለተኛ ምድብ ችሎት ቀርበው 14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸው ፍርድ ቤቱ በመፍቀዱ መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓ.ም. እንዲቀርቡ ታዟል፡፡
የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ለሪፖርተር እንደገለጸው፣ በአሥሩም ክፍላተ ከተሞች በቁጥጥር ሥር የዋሉት ተጠርጣሪዎች የመሬት አስተዳደር ኃላፊነትና የሥራ ድርሻ በመጠቀም፣ ሙስና ውስጥ ተዘፍቀዋል ተብለው በመጠርጠራቸው ነው፡፡
ኃላፊዎቹና ሠራተኞቹ የተጠረጠሩት የመንግሥት መሬት በሕገወጥ መንገድ ካርታ አዘጋጅቶ በመስጠት፣ ለልማት ሊወሉ የሚችሉ ቦታዎችን በግለሰብ ይዞታ በማካተት፣ በፍርድ ቤት ዕግድ የወጣባቸውን መሬቶች ያልታገዱ አስመስለው መረጃ በመስጠት፣ በሐሰተኛ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ስም ቦታ እንዲያዝ በማድረግ ወንጀሎች ነው፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በመሬት አስተዳደር ዘርፍ ያለውን ችግር ለመፍታት ባካሄደው ጥናትና ግምገማ፣ በ600 ሠራተኞች ላይ ዕርምጃ መውሰዱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
በዚህ ዕርምጃ በርካታ ሠራተኞች በአቅም ማነስ ምክንያት በሌሎች መዋቅሮች እንዲመደቡ፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሠራተኞች ደግሞ ከሥራቸው እንዲታገዱና እንዲሰናበቱ፣ እንዲሁም በሙስና ውስጥ ተሳትፎ እንዳላቸው በመረጃ የተረጋገጠባቸው ሠራተኞች ተጠያቂ እንዲሆኑ ውሳኔ ተላልፏል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ክላስተር አስተባባሪ አቶ አባተ ስጦታው የሚመራው ኮሚቴ፣ ተጠያቂ የሚሆኑ ሠራተኞች የተገኘባቸውን መረጃ በማጠናቀር ለፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ልኳል፡፡
በተወሰደው ዕርምጃ በሥራ ገበታቸው ላይ እንዳይገኙ በተደረጉ አመራሮችና ሠራተኞች ምትክ የሰው ኃይል ባለመመደቡ፣ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ክፍተት እየታየ መሆኑን ተገልጋዮች እየተናገሩ ነው፡፡
ሌሎች ተጨማሪ ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ሥር ለማዋል የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጋር በመሆን አደን መጀመሩ ታውቋል፡፡