በዓለም ላይ የታዳጊዎች የእግር ኳስ ፕሮጀክቶች በርካታ ከዋክብት በማፍራት ትልቅ ሚና ሲጫወቱ ይታያሉ፡፡ በቀደመው ጊዜ በየሠፈሩ እየተመለመሉ፣ ለክለብና ለብሔራዊ ቡድኖቻቸው ትልቅ ሚና ከተጫወቱ አንጋፋ ተጫዋቾች መካከል፣ የዓለም የኳስ ንጉሡ ፔሌና ጋሪንቻ ይጠቀሳሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜዎቹ ደግሞ ምትሐተኛው አርጀንቲናዊ ሊዮኔል ሜሲ አይታለፍም፡፡ ገና በለጋነቱ በፕሮጀክት ታቅፎ እያንከባለለ ያደገው ሊዮኔል ሜሲ፣ እንዲሁም ብራዚላዊው ሮናልዲኒሆ ጎቹና ፖርቱጋላዊው ክርስቲያኖ ሮናልዶ ወዘተ. ብዙዎቹን ከዋክብት በዚህ ረገድ መጥቀስ ይቻላል፡፡
ፕሮጀክቶች ገና ከጅምሩ ተሰጥኦና ፍላጎቱ ያላቸውን ታዳጊ ሕፃናትና ወጣቶችን በመመልመልና የኳስ ክህሎታቸውን ከተፈጥሮ ችሎታቸው ጋር በማዋሃድ ቀርፀው ሲያመጧቸው ይታያል፡፡ በኢትዮጵያም ኮፓ ኮካ ኮላ የመሰሉ ለዚህ የሚያበቁ ፕሮጀክቶችን በፋይናንስና መሰል ቁሳቁሶች በማገዝ አይነተኛ ሚና በመጫወት ላይ ይገኛሉ፡፡ ድርጅቱ ሰኔ 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ልደታ በሚገኘው የፋብሪካው ቅጥር ግቢ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ አራተኛውን ዓመታዊ የኮፓ ኮካ ኮላ ብሔራዊ የታዳጊ ወጣቶች የእግር ኳስ ውድድር መጀመር የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ተወካዮች በተገኙበት በይፋ አብስሯል፡፡
የኮካ ኮላ መጠጦች የምሥራቅ አፍሪካ ማኔጅንግ ዳይሬክተሩ ቫቪየር ሴልጋና የኮካ ኮላ የኢትዮጵያና የምሥራቅ አፍሪካ ብራንድ ማናጀር ወ/ት ትዕግሥት ጌቱ እንደተናገሩት ከሆነ፣ ‹‹የዘንድሮው የኮፓ ኮካ ኮላ የታዳጊዎች የእግር ኳስ ውድድር ከበፊቶቹ የበለጠና የተሻለ ይሆናል፡፡ ካለፉት ዓመታት ልምዶችን በመውሰድ የበቁ ታዳጊዎችን ማፍራት የሚቻልበት ዝግጅት እናደርጋለን፤›› ብለዋል፡፡ ድርጅቱ በተጨማሪም ለአዲስ ተመራጩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ አመራርና ለእግር ኳሱ ያለውን ድጋፍና ቁርጠኝነት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጧል፡፡ ምክንያቱም ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ አዲሱን አመራር ከመረጠ በኋላ የዚህ ውድድር መጀመር በተለይ ለኮፓ ኮካ ኮላ ጥሩ አጋጣሚ መሆኑንና በጋራ ውጤታማ ሥራ የሚሠሩበት ጊዜ እንደሚሆንም ተመኝተዋል፡፡
ብራንድ ማናጀሯ፣ ‹‹ኮፓ ኮካ ኮላ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ዕድገትና ስኬታማነት በቁርጠኝነት ይሠራል፡፡ በዚህ ረገድ ከፌዴሬሽኑ አዲሱ አመራር እንዲሁም ከብሔራዊ ወጣቶች አካዴሚ ጋር በመሆን ወጣቶችን የማፍራትና ወደ ፕሮፌሽናልነት የማሳደግ ጥረት በጉጉት የሚጠብቀው ነው፤›› ብለዋል፡፡
የዘንድሮ ኮፓ ኮካ ኮላ ውድድር ለሚቀጥሉት ሦስት ወራት በመላ አገሪቱ ዕድሜያቸው ከ15 ዓመት በታች ወጣቶች መካከል ይካሄዳል፡፡ እንደ ወጣው የውድድር መርሐ ግብር ከሆነ፣ የግራስ ሩትና የክልል አሸናፊዎች ከታወቁ በኋላ የውድድሩ ማጠቃለያ 11 የወንዶችና 11 የሴቶች የክልል ቡድኖችን በማገናኘት ለሳምንት ያህል በሚደረግ የኮፓ ሻምፒዮና ውድድሩ ፍጻሜውን ያገኛል፡፡