የኢትዮጵያ አሠሪዎች ኮንፌዴሬሽን ሼሕ መሐመድ አሊ አል አሙዲ ከእስር እንዲፈቱ የሳዑዲን መንግሥት እንደሚጠይቅ አስታወቀ፡፡
ከአገሪቱ ግንባር ቀደም አሠሪዎች መካከል አንዱ የሆኑት የሚድሮክ ኢትዮጵያ ሊቀመንበር ሼክ መሐመድ አል አሙዲ እንዲፈቱ ኮንፌዴሬሽኑ ብርቱ ፍላጎት ያለው በመሆኑ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ከጀመሩት ጥረት ጎን ለጎን ኮንፌዴሬሽኑም የራሱን ጥረት ለማድረግ በመነሳሳት ላይ መሆኑን ኮንፌዴሬሽኑ ሐሙስ ሰኔ 14 ቀን 2010 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ ገልጿል፡፡
የኮንፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ጌታሁን ሁሴን (ኢንጂነር) ጨምረው እንደገለጹት፣ ለሳዑዲ መንግሥት የሚያስገቡትን የይፈቱልን ጥያቄ የያዘ ደብዳቤ በቅርቡ ለሳዑዲ መንግሥት ይላካል፡፡
ከወር በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ከሳዑዲ ጉብኝታቸው በኋላ ባለሀብቱ እንደሚፈቱ የሳዑዲ መንግሥት ቃል እንደገባላቸው ቢያስታውቁም እስካሁን ባለሀብቱ ከእስር አልተፈቱም፡፡