የፖለቲካ መብቶችን አፍነዋል ተብለው የተለዩ ሕጎችን ለማሻሻልና መሠረታዊ የፍትሕ ሥርዓት ለውጥ ለማካሔድ የሚሠራ ብሔራዊ ምክር ቤት ተቋቋመ። ምክር ቤቱ “የፍትሕና የሕግ ሥርዓት ማሻሻያ ብሔራዊ ምክር ቤት” የሚል መጠሪያ የተሰጠው መሆኑን፣ በጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ ብርሃኑ ፀጋዬ ሰብሳቢነት እንደሚመራ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው የሪፖርተር ምንጮች ተናግረዋል።
ባለፈው ሳምንት የተቋቋመው ብሔራዊ ምክር ቤቱ 12 አባላት እንዳሉት፣ በሥሩም በስምንት ንዑስ ቡድኖች መደራጀታቸውን ለማወቅ ተችሏል። የምክር ቤቱ አባላት በመሆንም ከውጭ አገሮች የተመረጡ የሕግ ባለሙያዎች የተካተቱበት ሲሆን፣ ከአገር ውስጥም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የተመረጡ ባለሙያዎች፣ እንዲሁም በግል ሥራ የተሰማሩ የሕግ ባለሙያዎች እንደተካተቱበት ታውቋል።
የምክር ቤቱ አባላት በዜጎችና በሌሎች የውጭ አጋሮች የኢትዮጵያውያንን የፖለቲካ መብቶች አፍነዋል ተብለው ትችት ሲሰነዘርባቸው የቆዩ ሕጎች፣ ዓለም አቀፍና የኢትዮጵያን ነባራዊ ሁኔታ በማገናዘብና የአገሪቱን ብሔራዊ ደኅንነት በማያጋልጥ መንገድ ሊሻሻሉ የሚችሉበትን ሙያዊ ምክረ ሐሳብ በነፃነት እንዲያበረክቱ የሚጠበቅ መሆኑን ምንጮቹ ገልጸዋል።
የፀረ ሽብር አዋጁ፣ የበጎ አድራጎትና ሲቪል ማኅበራትና የሚዲያ አዋጆች ማሻሻያ እንዲደረግባቸውና ከተለዩ ሕጎች መካካከል ትኩረት የሚደረግባቸው እንደሆኑም ታውቋል።
የፍትሕ ሥርዓቱ በአገልግሎት አሰጣጥ ችግር የተተበተበ በመሆኑ ዜጎችን ለእንግልት፣ የፍትሕ ሥርዓቱን ደግሞ ለጥራት ችግር እንዳጋለጠው ለጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባካሄደው መለስተኛ ጥናት የተረጋገጠ መሆኑን የተናገሩት ምንጮች፣ መንግሥት የፍትሕ ሥርዓቱን ከመሠረቱ ለመለወጥ እንዲቻለው ከብሔራዊ ምክር ቤቱ ትልቅ ፋይዳ የሚኖረው ምክረ ሐሳብ በዋነኝነት እንደሚጠብቅ ገልጸዋል።
ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎት አለማግኘት፣ የፍርድ ውሳኔ ለማግኘት ለበርካታ ዓመታት መጉላላት፣ በወንጀል የተከሰሱ ሰዎች ከፖሊስ ምርመራ ጀምሮ ነፃ የሕግ አገልግሎት አለማግኘት፣ እንዲሁም ሥልጣንን መከታ በማድረግ ዜጎችን ማንገላታት የፍትሕ ሥርዓቱ መገለጫዎች መሆናቸውን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በተጠናው ጥናት የተለዩ መሆናቸውንም ምንጮች አክለዋል።
በመሆኑም ከብሔራዊ ምክር ቤቱ በዋናነት የዳኝነት ሥርዓት፣ ሕግ የማመንጨት፣ የማውጣትና የማሻሻል የአሠራር ሥርዓቶች፣ እንዲሁም የዴሞክራሲ ተቋማትን አሠራር በተመለከተ ምክር ቤቱ የማሻሻያ ምክረ ሐሳብ ለመንግሥት ማቅረብ እንደሚጠበቅበት ምንጮች ተናግረዋል።