ከወራት ውዝግብና ሽኩቻ በኋላ በቅርቡ የተመረጠው አዲሱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፈዴሬሽን አመራር የብሔራዊ ቡድን አሠልጣኝ ቅጥር ለመፈጸም ይፋዊ ማስታወቂያ አውጥቷል፡፡ ከሰኔ 19 እስከ ሰኔ 28 ቀን 2010 ዓ.ም. ድረስ ይቆያል በተባለው የቅጥር ማስታወቂያ፣ ተወዳዳሪዎች የካፍ ‹‹ኤ›› ላይሰንስ፣ ፕሪሚየር ሊጉን ጨምሮ በየደረጃው በሚገኙ ሊጎች አሥር ዓመት ማሠልጠንና ከዲፕሎማ በላይ የትምህርት ማስረጃ እንዲኖራቸው ይጠየቃሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ)፣ ከሦስት አሠርታት በኋላ ለደቡብ አፍሪካው የአፍሪካ ዋንጫ ተፎካካሪነት መብቃታቸውን ተከትሎ ከፍተኛ የእግር ኳስ ፍላጎትና ተነሳሽነት ተቀስቅሶ ቆይቷል፡፡ ይሁንና በወቅቱ የታየው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎና እንቅስቃሴ፣ ከእቅድ ይልቅ ስሜት ስለመራው ሁሉም ነገር ታሪክ ሆኖ እግር ኳሱ በተለይም በአሁኑ ወቅት የንትርክና የውዝግብ መድረክ ሆኖ ይገኛል፡፡ ከዚህም ሲሻገር ማዘውተሪያዎች ጎጥና መሰል እግር ኳሳዊ ወደ አልሆኑ አዝማሚያዎች እንዲቀየሩ ምክንያት ሆነዋል፡፡
ብዙ ተብሎለት የነበረው የዋሊያዎቹ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ፣ አንዳንዶች እንደሚናገሩት አቅምን ያላገናዘበ ፍላጎትና ስሜት አሁን ለሚገኝበት ውድቀት በዋናነት ተጠቃሽ ነው፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የቀድሞ አመራር፣ የወቅቱ የዋሊያዎቹ አለቃ የነበሩት አሠልጣኝ ሰውነት ቢሻውን በማሰናበት ኃላፊነቱን ለፖርቱጋላዊው ማሪያኖ ባሬቶ ቢያስረክብም፣ ዋሊያዎቹና ውጤት እንዲሁም ፍላጎትና ውጤት አልጣጣም ብለው መቆየታቸው ብቻ ሳይሆን የአሠልጣኙ የቆይታ ጊዜም እንዲያጥር ተደርጎ፣ በምትካቸው በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት አሜሪካዊ ለሆኑት አሠልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ፣ ከዚያም ሲቀጥል አሠልጣኝ አሸናፊ በቀለ እያለ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ እንዲቀጥሉ ቢደረግም የእነሱም ቆይታ በነበረው አመራር እንዲቋረጥ ተደርጎ፣ ዋሊያዎቹም አሠልጣኝ አልባ ሆነው ይገኛሉ፡፡
ብሔራዊ ቡድኑ ከአንድ ዓመት በኋላ ለሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ጋና፣ ኬንያና ሴራሊዮን በሚገኙበት ምድብ ይገኛል፡፡ ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ይህን ማስታወቂያ እስካወጣበት ድረስ ዋሊያዎቹ ያለ አሠልጣኝ ከሚገኙ ጥቂት የዓለም አገሮች ብሔራዊ ቡድኖች አንዱ ሆኖ እየተጠቀሰ ይገኛል፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ)፣ በ2020 የሚካሄደውን የአፍሪካ አገሮች ዋንጫ (ቻን)፣ ኢትዮጵያን በአስተናጋጅነት መምረጡ ይታወሳል፡፡
በመሆኑም የፌዴሬሽኑ አዲሱ አመራር የዋሊያዎቹን አለቃ ለመሰየም ይፋ ባደረገው የቅጥር ማስታወቂያ፣ ተወዳዳሪዎች ሊያሟሉ የሚገባቸውን መሥፈርቶች ቢያወጣም የወቅታዊ ብቃት ጉዳይ ከግምት እንዲገባ የሚጠይቁ አሉ፡፡ በዚህ ጉዳይ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የፌዴሬሽኑ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሰለሞን ገብረሥላሴ እንደተናገሩት ከሆነ፣ ጽሕፈት ቤቱ የብሔራዊ አሠልጣኙን የቅጥር ጉዳይ አስመልክቶ ምንም ዓይነት መግለጫ መስጠት እንደማይችል፣ ኃላፊነቱም ሙሉ በሙሉ የብሔራዊ ቴክኒክ ኮሚቴው እንደሆነ ጭምር ተናግረዋል፡፡ እንደ አስተያየት ሰጪዎቹ ከሆነ፣ በርካታ ቁጥር ያላቸው የካፍ ‹‹ኤ›› ላይሰንስ ባለቤት የሆኑ አሠልጣኞች አሉ፡፡ ይሁንና ከጥቂቶቹ በስተቀር ብዙዎቹ አሠልጣኞች በተለይም በአሁኑ ወቅት ክለብ ሳይዙ ያለ ሥራ ስለመቀመጣቸው ጭምር አልሸሸጉም፡፡