ከጦጣ ዝርያዎች አንዱና ‹‹ፕሮቦሲስ መንኪ›› ተብሎ የሚታወቀው ጦጣ በአፍንጫው አረዛዘም ታዋቂ ሆኗል፡፡ ፕሮቦሲስ ጦጣ የሚኖረው በትልቅነቱ ከዓለም ሦስተኛ ከእስያ አንደኛ በሆነው ቦርኒኦ ደሴት ነው። ደሴቱ የአገሩ ነዋሪዎች ይህን እንስሳ ኧራንግ ቤላንዳ ወይም “የደች ሰው” ብለው ይጠሩታል።
‹‹ንቁ!›› መጽሔት በ2012 ዕትሙ እንደገለጸው፣ እንደ ኩንቢ ጠልጠል ያለው የዚህ ጦጣ አፍንጫ በአንዳንድ ወንዶችች ላይ እስከ 18 ሴንቲ ሜትር ገደማ ሊያድግ ይችላል፡፡ ይህም የጦጣውን ቁመት (ጦጣው በአራት እግሮቹ ሲቆም) አንድ አራተኛ ያህላል ማለት ነው። የጦጣው የተንዘረፈፈ አፍንጫ አፉንና አገጩን ስለሚሸፍነው በሚበላበት ጊዜ አፍንጫውን ወደ ጎን ገፋ ማድረግ ይኖርበታል! የሰው ልጆች አፍንጫ ልክ እንደዚህ ጦጣ የቁመታቸውን አንድ አራተኛ የሚያህል ቢሆን ኖሮ ደረታቸው ዘንድ ይደርስ ነበር።
የፕሮቦሲስ ጦጣ አፍንጫ ጠቀሜታ አስመልክቶ ከተሰነዘሩት መላ ምቶች መካከል አንዳንዶች፣ አፍንጫው ከሰውነቱ ውስጥ ሙቀት እንዲወጣ በማድረግ ሰውነቱን ለማቀዝቀዝ እንደሚረዳው፣ አሊያም ኃይለኛ ድምፅ ለማውጣት እንደሚያስችለው ይገልጻሉ። አፍንጫውን ሌሎች ፕሮቦሲስ ጦጣዎችን ለማስጠንቀቅ እንደሚጠቀምበት የሚናገሩም አሉ። በእርግጥም የቡድኑ መሪ የሆነው አውራ በሚቆጣበት ወይም በሚፈራበትና በሚደነግጥበት ጊዜ አፍንጫው ይነፋና ቀይ ይሆናል። የተባዕቱ አፍንጫ፣ የእንስቷን ጦጣ ልብ ለመማረክም ሊያገለግል ይችላል።
ፕሮቦሲስ ጦጣዎች ከምድር ገጽ ለመጥፋት የተቃረቡ ዝርያዎች ዝርዝር ውስጥ ገብተዋል፤ ዋነኛ መኖሪያቸው በሆነው አካባቢ ያሉት ጦጣዎች በጥቂት ሺህዎች የሚቆጠሩ ሲሆኑ ቁጥራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሽቆለቆለ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ።