ባለፈው ሳምንት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተዘንግቷል የተባለለት የድሬዳዋ አስተዳደር የሥራ ዘመን ለማራዘም ሲጠበቅ የነበረውን ቻርተር ለማሻሻል የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅ፣ ማክሰኞ ሰኔ 26 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀረበ፡፡
በፓርላማው 33ኛ መደበኛ ስብሰባ ረቂቅ አዋጁ ተዘጋጅቶ የቀረበው በ2010 ዓ.ም. መከናወን የነበረበት የድሬዳዋና የአዲስ አበባ ምርጫ፣ በአገሪቱ ተከስቶ በነበረው አለመረጋጋት ምክንያት ባጋጠመው የፀጥታ ሥጋት ባለመካሄዱ ነው፡፡
ምርጫው ባለመካሄዱ የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤትን እንደገና ማደራጀት አይቻልም፡፡ የምክር ቤቱ የሥልጣን ዘመን ሰኔ 30 ቀን 2010 ዓ.ም. የሚጠናቀቅ በመሆኑ፣ የሕግ ማሻሻያ ማስፈለጉ ተገልጿል፡፡ ረቂቅ አዋጁ ሐምሌ 1 ቀን 2005 ዓ.ም. ሥራውን የጀመረው የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት፣ ምርጫው እስከሚካሄድ ድረስ ሥራውን እንዲቀጥል የሚያስችል ነው። ከዚህም በተጨማሪ ምክትል ከንቲባው ከምክር ቤት አባላት ወይም ከምክር ቤት ውጪ እንዲመረጥ ያስችላል ተብሏል።
ፓርላማው ሰኔ 21 ቀን 2010 ዓ.ም. ባካሄደው ስብሰባ በተመሳሳይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቻርተር ለማሻሻል በቀረበለት ረቂቅ አዋጅ ላይ መክሮ፣ ለተጨማሪ ዕይታ ለሕግ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መምራቱን መዘገባችን ይታወሳል።
ነገር ግን የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአዲስ አበባ አስተዳደር ምክር ቤትና የካቢኔ የሥራ ዘመን እንዲራዘም የሕጋዊነት ጥያቄ የተነሳበትን የሕግ ማሻሻያ ለማፀደቅ ለፓርላማው ሲልክ፣ በተመሳሳይ ጊዜ የሥራ ዘመኑን የሚያጠናቅቀው የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤትንና የሥራ አስፈጻሚ ካቢኔን እንደዘነጋው መዘገባችን አይዘነጋም፡፡
በዚህም ምክንያት የድሬዳዋ ከተማ ከንቲባ አቶ ኢብራሒም ኡስማን ዓርብ ሰኔ 22 ቀን 2010 ዓ.ም. አዲስ አበባ ተገኝተው፣ ከፌዴራል መንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ጋር መነጋገራቸውን ለሪፖርተር ገልጸው ነበር፡፡