Friday, December 1, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

የክቡር ሚኒስትሩ ሾፌር አርፍዶ ቤታቸው መጣ

[የክቡር ሚኒስትሩ ልጅ የፈተና ውጤቱን መጥቶ እያሳያቸው ነው፡፡ ክቡር ሚኒስትሩ በጣም ተናደዋል]

  • ና አንተ፡፡
  • አቤት ዳዲ?
  • ምን ሆነህ ነው?
  • ምን ሆንኩ?
  • ውጤትህን አይተኸዋል?
  • አሪፍ ነው አይደል ዳዲ?
  • ሳይንስ ያመጣኸው አሪፍ ነው፡፡
  • እንግሊዝኛስ ዳዲ?
  • እሱንም ጥሩ ሠርተሃል፡፡
  • የሶሻል ሳይንስ ውጤቴስ ጥሩ አይደል?
  • እኔ እሱ ላይ ጥያቄ የለኝም፡፡
  • ታዲያ ምን ላይ ነው ጥያቄ ያለህ?
  • ሒሳብ ላይ፡፡
  • ምንድነው ጥያቄህ?
  • ሒሳብ ላይ ያለብህ ችግር ምንድነው?
  • ኧረ ምንም ችግር የለብኝም፡፡
  • ታዲያ እንዴት ነው እንደዚህ ዓይነት ውጤት ልታመጣ የቻልከው?
  • ችግሩ የእኔ አይደለም ዳዲ፡፡
  • የፈተና ውጤትህን እያየሁት እኮ ነው?
  • ችግሩ የእኔ አይደለም አልኩህ እኮ ዳዲ፡፡
  • ከመቶ ስንት እንዳመጣህ አይተኸዋል?
  • እ. . . ዳዲ. . .
  • አሥራ አምስት በመቶ እኮ ነው ያመጣኸው?
  • እሱ እኮ የአስተማሪዎቹ ስህተት ነው፡፡
  • የምን የአስተማሪ ስህተት ነው፣ ስህተቱማ የአንተ ነው፡፡
  • አይደለም ዳዲ እኔ እንዲያውም ትምህርት ቤት ሄደን እንድታስረዳቸው ነው የምፈልገው፡፡
  • ምኑን ነው የማስረዳቸው?
  • መሳሳታቸውን ነዋ፡፡
  • የተሳሳትኸው አንተ ነህ እንጂ እነሱ እኮ አይደሉም፡፡
  • ዳዲ ሙት እመነኝ እነሱ ናቸው የተሳሳቱት፡፡
  • ወረቀትህን እያየሁት እንዴት እነሱ ተሳሳቱ ትለኛለህ?
  • አየህ ዳዲ አንተ ራስህ አልገባህም ማለት ነው?
  • ደግሞ ከመሬት ብቅ ሳትል እኔን ሒሳብ ልታስተምር ትፈልጋለህ?
  • ከተሳሳትክ ባስረዳህ ምን ችግር አለው?
  • ስለሒሳብ ሥሌት ነው እኔን የምታስረዳኝ?
  • ምን ችግር አለው?
  • ይኼ እኮ የሒሳብ መሠረታዊ ነገር ነው፡፡
  • አውቃለሁ ዳዲ፡፡
  • ብታውቅማ እንደዚህ አትሳሳትም ነበር፡፡
  • ዳዲ አንተም አስተማሪዎቹም ያልገባችሁ ነገር ስላለ ነው፡፡
  • ምንድነው ያልገባን?
  • የሒሳብ ሥሌት ነዋ፡፡
  • ቆይ እንጂ ከዘጠኝ ላይ ሦስት ሲቀነስ ስንት ነው?
  • አሥራ ሁለት፡፡
  • ሒሳብ ምንም አትችልም እንዴ?
  • እንዴ ዳዲ?
  • እሺ አሁን አራት ሲባዛ በሁለት ስንት ነው?
  • ስድስት፡፡
  • አሁን በደንብ ነው የገባኝ፡፡
  • ምንድነው የገባህ ዳዲ?
  • መሠረታዊ የሒሳብ ሥሌት ችግር እንዳለብህ፡፡
  • እኔ ደግሞ የገባኝ አንድ ነገር አለ፡፡
  • ምንድነው የገባህ?
  • አንተም አስተማሪዎቼም አዲሱን ለውጥ አትቀበሉም ማለት ነው፡፡
  • የምን ለውጥ?
  • አገሪቱ ውስጥ የመጣውን ለውጥ አትቀበሉትም ማለት ነው?
  • ፖለቲከኛም ሆነኸልኛል ልበል?
  • ዳዲ እኔ እንደተረዳሁት አንተም አስተማሪዎቼም የድሮ ሥርዓት ናፋቂዎች ናችሁ፡፡
  • እኔ ጠፋሁ፣ ከማን ጋር ነው የምትውልልኝ?
  • ዘመኑ የምን ዘመን መሆኑን ረሳኸው እንዴ?
  • የምን ዘመን ነው?
  • የመደመር!

[የክቡር ሚኒስትሩ ሾፌር አርፍዶ ቤታቸው መጣ]

  • አንተ ስለአዲሱ አለቃ ነግሬሃለሁ አይደል እንዴ?
  • አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • እንደዚህ እያስረፈድከኝ ልታስጠምደኝ ነው?
  • ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ይኼኔ ማታ አንቡላህን ስትልፍ አምሽተህ ነው፡፡
  • ኧረ በፍፁም፡፡
  • ምን ሆነህ ነው ታዲያ ያረፈድከው?
  • የዓለም ዋንጫ ሳይ አምሽቼ ነው፡፡
  • አሁን ምን ኳስ አለ ብለህ ነው?
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • አንጋፋዎቹ ቡድኖች ተባረው ምንም የዓለም ዋንጫ አይመስልም እኮ?
  • ዋናው እሱ አይደል እንዴ?
  • እንዴት ማለት?
  • አይነኬ የሚባሉት ቡድኖች እየተዋረዱ ምድባቸው እንኳን ሳይቀር ማለፍ ተስኗቸው ሲታዩ አያስገርምም?
  • ወጣት ሲባል እኮ ግንፍልተኛ ነው፡፡
  • እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
  • ስማ የዓለም ዋንጫን እኮ የዓለም ዋንጫ ያስባሉት ቡድኖች እነዚህ ናቸው፡፡
  • የትኞቹ?
  • እነ ጀርመን፣ ብራዚል፣ አርጀንቲና፣ ስፔንን የመሳሰሉት፡፡
  • ይኸው ከብራዚል ውጪ ሁሉም ከውድድሩ ተሰናብተዋል፡፡
  • ለዚህ ነው እኮ አንጋፋዎቹ የሌሉበት የዓለም ዋንጫ ምን የዓለም ዋንጫ ነው የምልህ?
  • ክቡር ሚኒስትር እነ ክሮሺያና ቤልጂየም የመሳሰሉ ቡድኖች ሲጫወቱ ግን አይተዋቸው ያውቃሉ?
  • የፈለገ ነገር ብትለኝ አንጋፋዎቹ የሌሉበት የዓለም ዋንጫ አንገሽጋሽ ነው፡፡
  • ሕዝቡ ግን ይኼኛውን የዓለም ዋንጫ በጣም በትኩረት ነው እየተከታተለ ያለው፡፡
  • እንደ አንተ ዓይነት ኳስ የማያውቅ ሰውማ ሊወደው ይችላል፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ከዘመኑ ጋር ሊለወጡ ይገባል እኮ፡፡
  • ምን ማለት ነው?
  • አንጋፋዎቹ እኮ ከውድድሩ የተባረሩት አዳዲሶቹ ላቅ ያለ የእግር ኳስ ችሎ ስላላቸው ነው፡፡
  • እንዳይመስልህ አትሳሳት፡፡
  • ታዲያ በምንድን ነው አንጋፋዎቹ የተባረሩት?
  • በአሻጥር፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ስመለከትዎ እርስዎ ከሚያውቁት ውጪ የሆነ ነገር አይወዱም፡፡
  • ምን እያልከኝ ነው?
  • ይኸው በአገሪቱ ውስጥ የመጣውን ለውጥ ራሱ መቀበል አይፈልጉም፡፡
  • አንጋፋዎቹ የሌሉበትን ለውጥ አልቀበለውም፡፡
  • እንደዚያ ከሆነ የእኔ ምክር አንድ ነው፡፡
  • ምንድነው ምክርህ?
  • በጊዜ ቢቆርጡ ይሻልዎታል፡፡
  • ምንድነው የምቆርጠው?
  • ትኬት ነዋ፡፡
  • የምን ትኬት?
  • የስንብት!

[ለክቡር ሚኒስትሩ በአገሪቱ አሸባሪ የተባለ ድርጅት አባል ከውጭ ስልክ ደወለላቸው]

  • ሰላም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ሰላም ነህ?
  • አገሪቱ ውስጥ ትክክለኛ ለውጥ መኖሩን እየተረዳሁ ነው፡፡
  • በምኑ ነው የተረዳኸው?
  • ስልኬን ራሱ ማንሳትዎ የለውጡ አካል አድርጌ ነው የቆጠርኩት፡፡
  • የምን ለውጥ ነው?
  • ይኸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ አገራችሁ መጥታችሁ ተደመሩ እያሉን አይደል እንዴ?
  • እንግዲህ እናንተ ስትደመሩ እኛ እንቀነሳለን፡፡
  • ምን ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • ለመሆኑ ሬሲሊንግ ዓይተህ ታውቃለህ?
  • በሚገባ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • አንድ ተፋላሚ ወደ ሪንጉ ሲገባ ሌላውን በእጁ እንደሚጨብጠው፣ እኛም እናንተ ስትገቡ ተጨባብጠን አገሪቱን ለቀን እንወጣለን፡፡
  • ለምን ክቡር ሚኒስትር?
  • እኔና አንተ ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ላይ መኖር አንችልም፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ዘመኑ የመደመር እኮ ነው?
  • በምንም ሥሌት እኔ ከአንተ ጋር ልደመር አልችልም፡፡
  • የድሮ ሥርዓት ናፋቂ ነዎት ልበል?
  • ነገርኩህ እኮ እኔና አንተ ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ላይ መኖር አንችልም፡፡
  • አይሳሳቱ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ማለት?
  • ኢትዮጵያ እንኳን ለእኔና ለእርስዎ ለሌሎች ትተርፋለች፡፡
  • ይኼን ፕሮፓጋንዳህን ወሬ ለተጠሙ ጓደኞችህ ንገራቸው፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር በፍቅርና በይቅርታ እኮ ለአገራችን ሰላም ማምጣት እንችላለን፡፡
  • ስማ ይኼው እዚህ ራሱ ያሰርናቸው አሸባሪዎች ተፈትተው ሰላም የነበረችው አገር እየተበጠበጠች ነው፡፡
  • እየቀለዱ ነው ክቡር ሚኒስትር?
  • የምን ቀልድ ነው?
  • ለሦስት ዓመታት አገሪቱ ታምሳ አሁን አይደል እንዴ ከመፍረስ የተረፈችው?
  • ስማ ለእኔ ግን ከነበረችበት የበለጠ ማጥ ውስጥ እየገባች ያለችው አሁን እየተደረጉ ባሉ ነገሮች ነው፡፡
  • አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር?
  • አሸባሪዎቹ ሲለቀቁ ሰላም የነበረችው አዲስ አበባ ውስጥ ቦምብ ፈነዳ፡፡
  • ቦምብ ያፈነዱት እኮ የለውጡ ተቃዋሚዎች ናቸው፡፡
  • አሸባሪን መልቀቅ ለውጥ ከሆነ እሱን ቢቃወሙ ምን ችግር አለው?
  • ክቡር ሚኒስትር እውነተኛ አሸባሪ እኮ መንግሥት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ  ተናግረዋል፡፡
  • የማልቀበለው እኮ ይኼንን ነው፡፡
  • ምኑን?
  • እኛ አሸባሪዎች እናንተ ሰላማዊ መሆናችሁን፡፡
  • ሀቁ ግን እሱ ነው፡፡
  • ስለዚህ እኛም የእናንተ ዕጣ እንዳይደርሰን በጊዜ እንወጣለን፡፡
  • ከየት?
  • ከአገር!

[ክቡር ሚኒስትሩ ፀጉር ቤት እየተስተካከሉ ከፀጉር ቆራጫቸው ጋር እያወሩ ነው]

  • ክቡር ሚኒስትር እንዴት ላድርገው ፀጉሩን?
  • እንደ ሁልጊዜው ነዋ፡፡
  • እኔማ ለወጥ ያለ ቁርጥ ልቆርጥዎት አስቤ ነበር፡፡
  • ሰውዬ ምንም ዓይነት ለውጥ አልፈልግም፡፡
  • ሽበትዎን ለማጥፋት ፈልጌ ነበር፡፡
  • ለምን ተብሎ?
  • ያው አርጅተዋል ምናምን ብለው ከፖለቲካው እንዳያባርርዎት ብዬ ነዋ፡፡
  • ማን ነው የሚያባርረኝ?
  • ክቡር ሚኒስትር እርስዎ ከተባረሩ እኔ ራሴ እጎዳለሁ፡፡
  • እንዴት?
  • የፀጉር ቤቴ ገቢ ሊቀንስ ይችላል፡፡
  • ለምን ይቀንሳል?
  • ያው አሁን ሚኒስትሩ የሚስተካከሉበት ፀጉር ቤት እየተባለ ገቢዬ ቀላል አይደለም፡፡
  • አንተ ግን ለእኔ ኮሚሽን አትከፍለኝም?
  • ይኸው አሁን በሚቀጥለው በጀት ዓመት የፀጉር ቤቴን ስም ሚኒስትሩ ፀጉር ቤት ልለው ወስኛለሁ፡፡
  • እሱ ምን ያደርግልኛል?
  • ያው አንጋፋዎቹ ለቀው በወጣት ይተኩ እየተባለ ስለሆነ፣ አንድ ሐሳብ ነበረኝ፡፡
  • የምን ሐሳብ?
  • እርስዎን ወጣት ማስመሰል እችላለሁ፡፡
  • እንዴት አድርገህ?
  • የፀጉርዎን ቀለም በመቀየር፡፡
  • እሱን ፈጽሞ እንዳታስበው፡፡
  • ለምን ክቡር ሚኒስትር?
  • ከተማ ውስጥ አዲስ አደን ተጀምሯል፡፡
  • ምንድነው የሚታደነው?
  • ፀጉረ ልውጥ!

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

- Advertisment -

ትኩስ ፅሁፎች

የመቃወም ነፃነት ውዝግብ በኢትዮጵያ

ስሟ እንዳይገለጽ የጠየቀችው በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ የሾላ አካባቢ...

የሲሚንቶን እጥረትና ችግር ታሪክ ለማድረግ የተጀመረው አጓጊ ጥረት

በኢትዮጵያ በገበያ ውስጥ ለዓመታት ከፍተኛ ተግዳሮት በመሆን ከሚጠቀሱ ምርቶች...

የብሔር ፖለቲካው ጡዘት የእርስ በርስ ግጭት እንዳያባብስ ጥንቃቄ ይደረግ

በያሲን ባህሩ በሪፖርተር የኅዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም. ዕትም “እኔ...

ሀብቱንና ትርፉን እያሳደገ የቀጠለው አዋሽ ባንክ

አዋሽ ባንክ በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ዋና መሥሪያ ቤት...
spot_img

ተዛማጅ ፅሁፎች

[ክቡር ሚኒስትሩ የሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ለተከበረው ምክር ቤት ካቀረቡ በኋላ ከምክር ቤቱ አባላት የሚነሱ ጥያቄዎችን እየተቀበሉ ማብራሪያ በመስጠት ላይ ናቸው]

ክቡር ሚኒስትር መንግሥት ለሕዝብ ይፋ ያደረገው ነገር ከምን እንደደረሰ ቢያብራሩልን? ምንድነው ይፋ ያደረገው? ጥያቄውን ትንሽ ቢያብራሩት? ከአራት ዓመት በፊት በኦጋዴን አካባቢ ነዳጅ መገኘቱን ለሕዝብ በቴሌቪዥን አብስሮ...

[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ የካቢኔና የማክሮ ኢኮኖሚ ኮሚቴ አባል የሆኑ ከፍተኛ አመራር የሚያቀርቡትን ቅሬታ እያደመጡ ነው] 

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር በእጅጉ ስላሳሰበኝ ነው በአካል አግኝቼ ላነጋግርዎት የፈለግኩት። ጥሩ አደረግህ፣ ምን አሳሳቢ ነገር ገጥሞህ ነው? ክቡር ሚኒስትር ተወያይተንና ተግባብተን ያስቀመጥናቸው አቅጣጫዎች፣ በተለይም...

[ጉባዔው በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ክቡር ሚኒስትሩን ለመጠየቅና ምላሽና ማብራሪያቸውን ለማድመጥ ተሰብስቧል። የጉባዔው አባላትም ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎቻቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር፣ ይህ ጉባዔ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ለመስጠት በመካከላችን ስለተገኙ አመሰግናለሁ። ክቡር ሚኒስትር፣ ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት የብሪክስ አባል እንድትሆን የሰጡት በሳል አመራር የሚደነቅ ነው። አገራችን...